Wednesday, January 14, 2015

ከሆቴሉ ጀርባ… በወላፈኑ ውስጥ የሚታየው – ፍጹምዘአብ አስገዶም ማን ይሆን?

ዘ-ሐበሻ 

  • 1637
     
    Share
bee392ccb91b968f78a29a035271c5d5_Lሰሞኑን የኢትዮጵያ ጥንታዊ ቅርስ የነበረው ጣይቱ ሆቴል በእሳት ወደመ:: ከዚሁ ጋር ተያይዞ ታዲያ “አቃጠሉት” እና “አቃጠሉበት” የሚሉት ድምጾች በርክተዋል:: “አቃጠሉበት” የሚለውን የጨዋታ ክር መምዘዝ ከጀመርን; የቤቱ ባለቤት ፍጹምዘአብ ጋር ያደርሰናል:: ፍጹምዘአብ የትግራይ ተወላጅ ነው:: ግን ደግሞ የትግራይ ተወላጅ ስለሆነ ከስልጣን ዙፋን ላይ አልተቀመጠም:: ይልቁንም በዘመነ ኢህአዴግ ከ6 አመታት በላይ የወያኔን እስር ቤትን ቀምሶ የወጣ ሰው ነው::
አሁን በተቃጠለው የጣይቱ ሆቴል ምክንያት ስለቃጠሎውም ሆነ ስለእቴጌ ጣይቱ ሆቴል ብዙ እየተባለ ነው:: ከዚህም በላይ ብዙ ሊባል ይችላል:: ምንም ተወራ ምን – ቢያንስ መሰረቱን እውነት ያደረገ ወሬ ይመረጣል:: ፍጹምዘአብ የትግራይ ተወላጅ ሆኖ የህወሃት ደጋፊም ተቃዋሚም ስላልሆነ እንደማንፈርድበት ሁሉ – የነጻ ፕሬስ ተጋድሎውን ብዙ በመታሰር እና ባለመታሰሩ ኢትዮጵያዊነቱን ልንለካው አንችልም:: እንደ’ውነቱ ከሆነ; ዘ ሞኒተር ጋዜጣን በሳምንት ሶስቴ ከመታተም አልፎ በየቀኑ የሚታተም የመጀመሪያ እንግሊዘኛ ጋዜጣ እንዲሆን አድርጓል:: ጋዜጣው ከዘመኑ ጋር እንዲሄድ ብቻ ሳይሆን የራሱ ማተሚያ ቤት እንዲኖረው ማድረጉ በራሱ፤ መጋነን ባይገባውም በነጻው ፕሬስ ታሪክ ውስጥ ስፍራ ሊሰጠው ይገባል::
(ዳዊት ከበደ ወየሳ)
ፍጹምዘአብን የምናውቀው ከመጀመሪያዎቹ የኢትዮጵያ ነጻ ፕሬስ ጋዜጦች አንዱ የሆነውን “ዘ ሞኒተር” ጋዜጣ አሳታሚ ሆኖ ሲሰራ ነው:: እኛ የነጻው ፕሬስን የነጻነት ብዕር ይዘን ባማርኛ ስንውተረተር – ፍጹምዘአብ በእንግሊዘኛ የሚታተም ዘሞኒተር ጋዜጣን ተረጋግቶ ያሳትም ነበር:: የነበረውን መንግስት የሚቃወም ወይም ያለፈውን የደርግ ስርአት የሚያወግዝ ጽሁፍ እምብዛም በጋዜጣው ላይ አይነበብም:: ሁሉንም ነገር በጥንቃቄ ለመያዝ ይሞክራል:: ከዚህም ከዚያም ጋር እየሄደ አይላተምም:: እኛ ኢህአዴግ ያጠመደውን የፕሬስ ነጻነት አልፈን፤ ፈንጂ ወረዳውን እየረገጥን ስንረጋገጥ – ፍጹምዘአብ ግን በጩኸት እና በትርምሱ መሃል በጥንቃቄ መራመድን ያዘወትር ነበር:: እንደዛም ሆኖ ግን ከህወሃት ሰዎች የጥላቻ አይን ሊወጣ አልቻለም::
የኢትዮጵያ ነጻ ፕሬስ ጋዜጠኞች ከየቢሯቸው እየተለቀሙ ከታሰሩባቸው ጊዜያት መሃል፤ የፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ እና አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የተነሳው አመጽ ጉዳይ ይጠቀሳሉ:: (እ.ኢ.አ. 1984 እና 1985)
በዩኒቨርስቲው ዘገባ ጉዳይ እኔም ተከስሼ ጉዳያችን ከነሙሉጌታ ሉሌ እና ከነመጽሃፈ ሲራክ መዝገብ ጋር በጠቅላይ ፍርድ ቤት ችሎት ይታይ ነበር:: ይሄ የአንድ ሰሞን ወሬ እንዳለፈ ደግሞ ሌላ ዙር ወሬ መጣ – በዙምባብዌ ኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማርያም ላይ የተደረገው የመግደል ሙከራ የፕሬሱን ገጾች አጣበበ::
በዚህ አዲስ የወሬ ዙር የነፍጹምዘአብ ዘ ሞኒተር ጋዜጣ የፕሬሱን የፈንጂ ወረዳ ረገጠ:: እናም ለሁሉም ጋዜጠኛ የተዘጋጀውን እስር ቤት አብሮን ለመጋራት በቃ – 1988::
ይህ እስር በጥንቃቄ መራመድ ለሚያዘወትረው ፍጹምዘአብ አስገዶም የማንቂያ ደወል ነበር:: እዚህ ላይ ዝርዝሩ ጥቅም የለውም እንጂ አስቀድማ የታሰረችው የጋዜጣው አዘጋጅ ሉሊት ነበረች:: እሷ ወሬውን የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ኢቲቪ እና ሬድዮ ጭምር መዘገቡን ለመርማሪው ታስረዳለች::
መርማሪው መልሶ ይጠይቃታል “እኮ አንቺ ዜናውን ከየት አገኘሽው?”
“ኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ካገኘበት ነዋ”
“ማነው ኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት?”
ሉሊት ማስረዳቷን ቀጠለች፤ “የመንግስት ዜና አገልግሎት ነው:: እነሱ ዜናውን ከፓን አፍሪካ ኒውስ እና አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ነው ያገኙት:: እኛም እንደነሱ ወርሃዊ ክፍያችንን ስለምንፈጽም የፓናፍሪካ እና የአጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዜናዎች ይደርሱናል” …ሉሊት እና መርማሪው ሊግባቡ አልቻሉም:: እንዲያውም መርማሪው ከአቅሙ በላይ ስለሆነበት ጉዳዩን ለበላይ ሃላፊዎቹ አስተላለፈ:: የበላይ ሃላፊዎች ደግሞ የጋዜጣው አሳታሚ ፍጹምዘአብ ተጨምሮ እንዲታሰር አደረጉ – ያን ግዜ እሱ እና እኛ በእስር ቤት እኩል ሆንነ :)
ያኔ የፍጹምዘአብ እድሜ ገና በሰላሳዎቹ መጀመሪያ ላይ ስለነበር እድሜያችን ሃያ + ለነበርነው እንደታላቅ የሚታይ ነው:: ለነገሩ በሁኔታው የራዕይ ገንቦ ተሸክሞ የሚሄድ ይመስላል። በዚያን ኢንተርኔት እና ማህበራዊ ድረ ገጾች በኢትዮጵያ ቀርቶ በአፍሪቃ ባልተስፋፋበት ዘመን እሱ ከዘመኑ ጋር ለመራመድ ዳዴ ማለቱን ጨርሷል:: እኛ በሳምንት አንድ ጊዜ የምናሳትማት ጋዜጣ በአፈና ጫና ስር ሆና ስትንፈራፈር – እሱ ወደፊት በኢትዮጵያ የህትመት ብቻ ሳይሆን፤ የግል ኤሌክትሮኒክስ መገናኛዎች መስፋፋት እንዳለባቸው ጥልቅ ትንታኔ ይሰጥ ነበር:: ሆኖም ያቺ አጭር የእስር ዘመን ፍጹምዘአብ አይኑን ገልጦ በኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን የህወሃት አምባገነን ስርአት እንዲመለክት የረዳው ይመስላል::
ታሪኩን ለማሳጠር ያህል ሉሊትም ሆነች ፍጹምዘአብ በኋላ ላይ በአስር ሺህ ብር ዋስ ሲወጡ ጋዜጣቸው ለአንድ ወር ያህል ከህትመት ታግዶ ነበር:: በቀጣይ ግዜያቶች… ዘ ሞኒተር ጋዜጣ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ጉዳዮችን እንደጾመ ቀጠለ:: ሆኖም በሚገርም ሁኔታ የነጻ ፕሬስ ጋዜጠኞች ሲታሰሩ ጉዳያቸው በውጭ ቋንቋ ተመንዝሮ የሚጻፍበት ብቸኛው እንግሊዘኛ ጋዜጣ ዘ ሞኒተር እንደነበር በፕሬስ ጉዳይ ታስረን የወጣን ሰዎች ሁሌም የምናስታውሰው ነው:: በኋላ ላይ እንደሰማሁት… ሌሎች ጋዜጠኞች ዲ አፍሪክ ጋር በነበረው አርቲክራፍት በተባለ ማተሚያ ቤቱ ያውቁታል – ያመሰግኑታል::
ጋዜጣም ሆነ መጽሄት ለማሳተም ወደዚህ ማተሚያ ቤት የሄድንበት አጋጣሚ የለም:: ሆኖም የኋላ ኋላ የመንግስት ማተሚያ ቤቶች ሲያስቸግሩ የነጻው ፕሬስ ልጆች ወደዚህ ማተሚያ ቤት ሄደው ያሳትሙ እንደነበር – በቅርቡ ከወጡት ጋዜጠኞች መካከል ሰርካለም ፋሲል አስታውሳኛለች::
ፍጹምዘአብ አስገዶም ብዙ የማያወራ ብቻ ሳይሆን በአደባባይ ልታይ ልታይ ማለትን የሚያዘወትር አይደለም:: ውስጡ ሁልጊዜም በዝምታ የተወጠረ እና መቼ እንደሚፈነዳ በማይታወቅ እሳተ ጎመራ የታመቀ ነው:: በዚህ የሰከነ ስሜት ውስጥ ያለ ሰው በፖለቲካ ምህዋር ዙሪያ ሊሽከረከር ቀርቶ – በዚያ ዙሪያ የሚሽከረከሩትንም በሩቁ ከማየት ውጪ እምብዛም ተሳትፎ አያደርግም:: ነገር ግን ምንም ቢጠነቀቅ የፖለቲካው በትር አናቱን ሳይመታው አያልፍም። ምንም ስሙን እና ማንነቱን ቢደብቅ – ማን እንደለኮሰው በማይታወቅ የእሳት ወላፈን መሃል በጭላንጭልም ቢሆን እናየዋለን – ፍጹምዘአብ አስገዶምን::
እንግዲህ ነገሮች በዚህ አይነት አለፉና መታሰር አይቀርም – በ5ኛ አመቱ እንደገና የሚታሰርበት ጊዜ መጣ። በነስዬ አብርሃ ላይ ጥርስ የነከሰው ህወሃት – የነሱ ተባባሪ ያላቸውን ሰዎች በሙስና ሰበብ ማሰር ጀመረ። የሙስናው ምንጭ የተባለው ደግሞ የአቶ ስዬ አብርሃ ታናሽ ወንድም “አሰፋ አብርሃ” መሆኑ ነገሩን ከፍ አደርገው። እኛ በጋዜጣችን ላይ የአቶ አሰፋ አብርሃን የሙስና ጉዳይ ስናነሳ፤ “የክቡር አቶ አሰፋ አብርሃን ስም በማጥፋት…” ተብሎ፤ አንቀጽ ተጠቅሶ፤ እውነት መናገር ወንጀል ሆኖ፤ መንግስት በፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 1ኛ ችሎት ከሰሰን። በሚገርም ሁኔታ ግን… የኛ ፋይል ሳይዘጋ አቶ አሰፋ አብርሃን መንግስት ራሱ ከሰሳቸው። ይህን እንደምሳሌ ማንሳት ያስፈለገው – ሰው የኢህአዴግ መንግስት ደጋፊ እስከሆነ ድረስ በሙስና ጭቃ ውስጥ ተዘፍቆ መኖር ይችላል። ከመንግስት ጋር የሚያጣላውን ነገር ከሰራ ግን፤ ስሙ በጥቁር መዝገብ ላይ ሰፍሮ ወደ እስር ቤት ይወረወራል።
ፍጹምዘአብ አስገዶም በፕሬሱ ውስጥ ያደረገው አስተዋጽኦ እንዳለ ሆኖ የትዳር እና የንግድ ህይወቱን በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ ከነአሰፋ አብርሃ ጋር አቆራኝቶታል። በአንድ በኩል የፍጹምዘአብ ባለቤት የአሰፋ አብርሃ ታናሽ እህት ናት። በሌላ በኩል ደግሞ ጨረታ እያሸነፈ ያገኛቸው የንግድ ቦታዎች በአሰፋ አብርሃ ፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ የተሸጡ የቀድሞ መንግስት ንብረቶች ናቸው። እነዚህም የጉለሌ ሳሙና ፋብሪካ፣ የሃረር ማተሚያ ቤት እና የጣይቱ ሆቴል ናቸው። ከሁሉም ግን የጣይቱ ሆቴል ጉዳይ ጎልቶ በነጻው ፕሬስ ላይ የመነጋገሪያ አጀንዳ ሆኖ ሰንብቶ እንደነበር ብዙዎች እናስታውሳለን።
ፍጹምዘአብ አስገዶም ጣይቱ ሆቴልን የገዛው በ425 ሺህ ብር ሲሆን፤ በወቅቱ ብቸኛው ተጫራች ሆኖ ነበር ጨረታውን ያሸነፈው። የተገዛበት ዋጋ ዛሬም ድረስ እንደአስደናቂ ታሪክ መወራቱ ቀጥሏል። ምክንያቱም እንኳንስ ጣይቱ ሆቴል ከነግቢው ቀርቶ፤ በሆቴሉ የላይኛው ክፍል ውስጥ ያለው በ19ኛው ክፍለዘመን ዝነኛ የነበረው የ1889 ስቴንዌይ ፒያኖ ግማሽ ሚሊዮን ብር ያወጣልና። ይህም ሆቴሉ ከተገዛበት ዋጋ ጭምር ያነሰ ነው። እናም ይህ ለማመን የሚያስቸግር ዋጋ – ለፍጹምዘአብ እንደሎተሪ ማሸነፍ የሚቆጠር ነበር። በወቅቱ ነጻው ፕሬስ ውስጥ ያለነውም ሆንን ባህል ሚንስቴር ውስጥ ያሉ አንዳንድ ሰዎች፤ “ጣይቱ ሆቴል በቅርስነት መጠበቅ ያለበት እንጂ፤ ሊሸጥ የሚገባው ንብረት አይደለም።” ብለው እና ብለን ድምጻችንን አሰማን። ሆኖም የሚሰማን ጠፍቶ ጣይቱ ሆቴል ተሸጦ እ.ኢ.አ. ሰኔ 21 1991 ዓ.ም. ርክክቡ ተፈጸመ – የኛም ጩኸት የአንድ ሰሞን ጫጫታ ሆነና ሁሉም ነገር ከግዜው ጋር ተረሳ።
ይሄ ጩኸት ሌላ ትርጉም እስካልተሰጠው ድረስ የቅናት እና የምቀኝነት አልነበረም። ሰሚ ጠፋ እንጂ… ጩኸታችን የኢትዮጵያን ቅርስ ከመጠበቅ አንጻር የሚታይ ነው። ጣይቱ ሆቴል ጥንታዊነቱን ጠብቆ በቅርስነት መጠበቅ ሲገባው እንደሸቀጥ መሸጥ አይገባውም ነበር – የኛ ክርክር። እርግጥ ነው – ጉለሌ ሳሙና ፋብሪካን ከ22 ሚሊዮን ብር በላይ ጨረታ አሸንፎ፤ ከአንድ አመት በፊት ለገዛው ፍጹምዘአብ የጣይቱ ሆቴል ዋጋ አነስተኛ መሆኑ ጥያቄ ውስጥ የሚገባ አይደለም። ሌላው ቀርቶ አሁን ጣይቱ ሆቴል ሲቃጠል የጃዝ-አምባ የሳውንድ ሲስተም እና የሙዚቃ መሳሪያ አብሮ ወድሟል። ስራ አስኪያጁ ኤርሚያስ ፋንቱ እንዳለው ከሆነ፤ “በትንሹ የ4 ሚሊዮን መሳሪያ በቃጠሎው ጠፍቶብናል” ብሏል። ጣይቱ ሆቴል የተገዛበትና የጠፋውን ንብረት ስናነጻጽረው… “የስሙኒ ዶሮ የአንድ ብር ገመድ ይዛ ጠፋች” የሚባለውን ተረት ያስታውሰን ጀምሯል።
ነገርን ነገር እየመዘዘ ወደ ታሪኩ ማጠቃለያ ልንቃረብ ሆነ። ወደኋላ እንመልሳችሁ እና አንዳንድ ነጥቦችን እናንሳ። በዛው ከላይ የጀመርነውን ጨዋታ መስመር እናስይዘው።
…ከዛ በኋላ… ስዬ አብርሃ ከነመለስ ዜናዊ ጋር ስለተጣላ በሙስና ሰበብ ታሰረ። ታናሽ ወንድሙ አሰፋ አብርሃ – በጠቅላይ ሚንስትርነት ማዕረግ – የፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ ሃላፊ እና የንግድ ባንክ ቦርድ ሰብሳቢ ሆኖ ሲሰራ፤ የፈጸመው ሙስና አለ ተብሎ እሱም ታሰረ። ፍጹምዘአብም “ከአሰፋ አብርሃ ጋር ያለውን ግንኙነት በመጠቀም ጉለሌ ሳሙናን፣ ሃረር ማተሚያ ቤት እና ጣይቱ ሆቴልን ገዝቷቸዋል” የሚል ክስ ተመሰረተበት።
እርግጥ ነው። ፍጹምዘአብ ከመታሰሩ በፊት… ጣይቱ ሆቴልን እያደሰው ነበር። ከታች ለደንበኞች አገልግሎት ይሰጥ የነበረው ቦታ እንዳለ ነው። ከሱ በላይ የነበረው ፎቅ ደግሞ የቀድሞ ሰራተኞች ያድሩበት የነበረ ስፍራ ነው። በኋላ ላይ… እድሳት አድርጎ፤ የፎቁን ቦታ ለእስዕል ጋለሪ እንደሚጠቀምበት ስንሰማ “ይሁን” አልነ። ፍጹምዘአብም ቢሆን ቢሮውን እዚሁ ጣይቱ ሆቴል አድርጎ፤ በየእለቱ የሚወጣውን የዴይሊ ሞኒተርን ጉዳይ የሚከታተለው ከዚሁ ከጣይቱ ሆቴል ሆነ። ሆኖም ሆቴሉንም በገዛው በ2ኛው፤ ጋዜጣውም በተመሰረተ በ10ኛ አመት ታሰረ።
በሚገርም ሁኔታ… ፍጹምዘአብ የታሰረው ከአሰፋ አብርሃ ጋር በነበረው ግንኙነት የሙስና ክስ ተመስርቶበት ቢሆንም፤ ሰዎቹ ግን አጋጣሚውን በመጠቀም The Daily Monitor ጋዜጣን ዘጉ። በኋላ ላይ ፍጹምዘአብ “የጋዜጣው መዘጋት ከተከሰስኩበት ጉዳይ ጋር ግንኙነት ስለሌው፤ ጋዜጣው ስራውን እንዲቀጥል፡” ብሎ ለፍርድ ቤቱ ስሞታ ቢያቀርብም የሚሰማው አጥቶ ጋዜጣው እና የጋዜጣው ቢሮ ተዘግተው ቀሩ።
በኋላ ላይ ፍጹምዘአብ ለአምስት አመታት እድሜውን በእስር ቤት አሳለፈ። መጨዋወታችን ካልቀረ “የባከነው ግዜ” ብለን አጭር ርዕስ እንስጠውና… ከእስር የተፈታበትን አጋጣሚ እናውጋ። ዋናው አጨቃጫቂ ጉዳይ የሆነው የጉለሌ ሳሙና ፋብሪካ ጉዳይ ነበር። በእርግጥ ሃረር ማተሚያ ቤት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ንብረት ሆኖ ሳለ፤ በደርግ ዘመን ተወርሶ የመንግስት ንብረት ሆነ። በኋላ ላይ… በኢህአዴግ ዘመን ቤተ ክርስቲያኗ ማተሚያ ቤቱ እንዲመለስላት አመልክታ ሳለ፤ ሃረር ማተሚያ ቤት ለጨረታ ቀርቦ… ፍጹምዘአብ የወሰደው።
አወዛጋቢው የጨረታ ድራማ የተፈጸመው ግን በጉለሌ ሳሙና ፋብሪካ ላይ ነው። ዱጉማ ሁንዴ እና ጌቱ ገለቱ የተባሉ ትላልቅ ባለሃብቶች ፋብሪካውን ሙሉ ለሙሉ ለመግዛት 21 + ሚሊዮን ብር ይጫረቱና እ.ኢ.አ በ1989 ጨረታውን ያሸንፋሉ። ማሸነፋቸውም ይነገራቸዋል።
ሆኖም ዱጉማ ሁንዴ እና ጌቱ ገለቱ የአሸናፊነት ጽዋቸውን አንስተው ደስታቸውን ከማጣጣማቸው በፊት ደስ የማይል ወሬ ይሰማሉ። ቦርዱ ውሳኔውን ቀይሮ ‘22 ሚሊዮን ብር እና ፋብሪካውን በከፊል ባለቤት ለመሆን የተጫረተው ፍጹምዘአብ የሳሙና ፋብሪካውን እንደሚወስድ ሰምተው አዘኑ። (ከከፊል ባለቤትነት ወደ ሙሉ ይዞታንነትም ተቀየረ) ሆኖም እነዱጉማ ሁንዴ ሌላ በሚሊዮን እና በቢሊዮን የሚቆጠር ቢዝነስ ውስጥ ስለነበሩ፤ “ፋብሪካው ለፍጹምዘአብ አስገዶም ለምን ተሰጠ?” የሚል የመጨቃጨቂያ ርዕስ ከፍተው ለመካሰስ ግዜ አልነበራቸውም። በአጭሩ ጥር 5ቀን፣ 1989 ፋብሪካው ለፍጹምዘአብ ተሸጠ። አራት አመታትም ተቆጠሩ። ከዚያም በህወሃት ውስጥ የርስ በርስ ጦርነት ሲከፈት የተጠመዱት ፈንጂዎች… ከዚህም ከዚያም ይፈነዳዱ ጀመር። በዚህ አጋጣሚ የአገራችንን የፍትህ ጉድለት ያሳያልና የሳሙና ፋብሪካውን ጉዳይ ብቻ እዚህ ላይ ጠቅሰን፤ ስለጣይቱ ሆቴል ትንሽ አውግተን ማሳረጊያ እናደርጋለን።
ላለፉት አራት አመታት ምንም ኮሽ ሳይል… ሳሙናው እየተመረተ ህዝቡ በጉለሌ ሳሙና ልብሱን ማጠቡን ቀጥሏል። ዘ ሞኒተር ጋዜጣም አዲስ በተገዛው ማተሚያ ቤት በየቀኑ እየታተመች ስሟን ቀይራ The Daily Monitor ተብላለች። አዲሱ እስር ሲመጣ ሳሙናው እየተመረተ ልብሳችንን እንጠብ እንጂ፤ ውስጣችንን የሚያጥበው የእንግሊዘኛ ፕሬስ ውጤት ግን እንደተዘጋ ቀረ።
ከርዕሳችን ላለመውጣት ያህል ወደ ሳሙና ፋብሪካው እንመለስ። እናም ጉለሌ ሳሙና በስራ ላይ ሳእ፤ በአራተኛ አመቱ አቃቤ ህጉ “ግዢው ህገ-ወጥ ነው” በማለት ክስ መሰረተ። የከሳሹ አቃቤ ህግ ጭብጥ የነበረው፤ “ፍጹምዘአብ ሳሙና ፋብሪካውን በ22 ሚሊዮን ብር ሲገዛው፤ በህጉ መሰረት 40 ፐርሰንት ለባንኩ ተቀማጭ ማድረግ ነበረበት። እሱ ግን ዜሮ ተቀማጭ በማድረግ ሳሙና ፋብሪካውን ወሰደ።” የሚል ሲሆን፤ ከዚህ ጋር በተያያዘ ከአሜሪካ አገር ኒው ዮርክ ከተማ መጥቶ የመንግስት ፋይናንስ አማካሪ ሆኖ ከቆየ በኋላ የብሄራዊ ባንክ ስራ አስኪያጅ የነበረው አላዛር ደሴ ጭምር እስር ቤት ገባ። ለነገሩ አላዛር ደሴ በዚህ ምክንያት ይታሰር እንጂ፤ የእስሩ ዋና ምክንያት ወዲህ ነው።
ከአምስት አመታት በኋላ…
አቃቤ ህጉ በፍጹምዘአብ ላይ ምስክር አቀረበ። አንደኛው እና ዋነኛው ምስክር የባንኩ ኦዲተር ነበር። እናም ፍጹምዘአብ ማስቀመጥ ሲገባው ስላላስቀመጠው 40 ፐርሰንት ተቀማጭ ጉዳይ ተጠየቀ። ኦዲተሩ ግራ በመጋባት፤ “አረ አስቀምጧል።” አለ።
“አርባ ፐርሰንቱን ለባንክ ከፍሏል?” ዳኛው በመገረም ጠየቁ።
“አዎ ተከፍሏል። ይኸው መረጃው!” ፍጹምዘአብን የሚረዱ፤ 8.9 ሚሊዮን ብር የከፈለበት መረጃ ቀረበ።
አቃቤ ህጉ ገና ከመጀመሪያው መከራከሪያ ያደረገው “አርባ ፐርሰንት አልከፈለም” የሚለው ጉዳይ እዚህ ላይ አበቃ። መንግስትን በመወከል የሚከራከሩት አቃብያነ ህጎች ‘ኩም’ አሉ – አፈሩ። ፍርድ ቤቱም በፍጹምዘአብ ጉዳይ የዚያኑ ቀን ውሳኔ ሰጠ። “ፍጹምዘአብ ከዛሬ ጀምሮ በዚህ ጉዳይ ነጻ ነው” ሲል አሰናበተው። ይህ የሆነው በኢትዮጵያ አቆጣጠር ጥር 11 ቀን፣ 1998 (የዛሬ ዘጠኝ አመት ነው)
ፍጹምዘአብ ሲታሰር እንጂ ሲፈታ አገር ውስጥ ስላልነበርኩ ዝርዝር ታሪኩን እንዘለዋለን። በዚያው ዝላይ ወደድሮ ታሪክ እንሸጋገራለን።
የጣይቱ ሆቴል ነገር ሲነሳ ትንሽ ወደ ኋላ ተመልሰን በዘመኑ ዘመነኛ ስለነበረው ሆቴል ማሰባችን አይቀርም። ወደ ኢትዮጵያ የሚመጡ የውጭ አገር ሰዎች የሚያርፉበት ሆቴል አለመኖሩ፤ ሌላው ቀርቶ ከፍለው እንኳን የሚበሉበት ምግብ ቤት አለመኖሩ ያሳሰባቸው አጼ ምኒልክ ናቸው – ሆቴሉ እንዲሰራ ያደረጉት። ሆኖም ከቤት ውጪ – ሊያውም ገንዘብ ከፍሎ መብላት ስላልተለመደ ወደ ጣይቱ ሆቴል መሄድ አይዘወተርም ነበር። በኋላ ግን እንዲህ ሆነ።
አንድ እሁድ ቀን ከቤተ ክርስቲያን መልስ አራዳ ጊዮርጊስ ከሚገኘው (አሁን የአጼው ሃውልት ካለበት ስፍራ) ዋርካው ስር ችሎት ቆይተው ሲጨርሱ፤ እዚያ የነበሩትን ባላባት እና መኳንንት፤ “በሉ ከጣይቱ ሆቴል ሄደን ምሳችንን እንብላ” አሏቸው።
መኳንንቱ በፈረስ እና በበቅሎ ተከታትለው አዲስ ከተሰራው ጣይቱ ሆቴል አመሩ።
ምግብ ከመብላታቸው በፊት፤ አጼ ምኒልክ አሉ፤ “በውጭ አገር እንዲህ ያሉ ሆቴሎች ይሰሩና ሰዎች ይመገባሉ” አሏቸው። አሉና እየተበላ እና እየተጠጣ ጨዋታው ደራ።
በመጨረሻ… ከተመገቡ በኋላ የበሉት እና የጠጡት ተሰልቶ ሂሳብ ቀረበላቸው። መኳንቱ ባልጠበቁት ነገር ተገርመው ሊቆጡ የቃጣቸውም ነበሩ። ምኒልክ ግን አሉ፤ “አያቹህ… በውጭ አገር ሰው ሆቴል ከተመገበ በኋላ ሂሳብ ይከፍላል” አሉና ገንዘብ አወጡ።
ነገሩ የምር እንደሆነ ያወቁት መኳንንት፤ “የለም። መክፈል ካለብንም እኛ እንከፍላለን እንጂ፤ እርስዎ አይከፍሉም።” አሏቸው። ሂሳቡን መክፈል የሚፈልጉት ሰዎች ብዛት ሲጠየቅ ይሄም ያም እየተነሳ፤ “ዘራፍ ደሞ ለ’ቴጌ” እያለ ለመክፈል ይጋበዝ ጀመር። አጼ ምኒልክም ለመክፈል የሚጋበዙትን መኳንንት ካዩ በኋላ፤ “እንግዲህ በውጭ አገር…” ብለው ጀመሩ፤ ሁሉም ዝም ብሎ ይሰማ ጀመር።
“እንግዲህ በውጭ አገር እንዲህ በልተው፤ አንድ ሰው ሂሳብ ከከፈለ፤ ሌላው ደግሞ በተራው በሚቀጥለው ሳምንት ይከፍላል” አሏቸው። ከዚያን በኋላ በየሳምንቱ እንደ እቁብ ጣይቱ ሆቴል እየተገኙ ምሳ መገባበዝ ተለመደ። ፈረንጆችም ወደ ኢትዮጵያ ሲመጡ የሚያርፉበት እና የሚመገቡበት የመጀመሪያው ዘመናዊ ሆቴል ሆነ።
አጋጣሚውን በመጠቀም ስለ ጣይቱ ሆቴል ይቺን እንመርቅ። በሁለተኛው የኢትዮጵያ ጣልያን ጦርነት ወቅት – በጄነራል ፔትሮ ባዲዮ (በኋላ ላይ ማርሻል ሆኗል) የሚመራው ጦር ወደ አዲስ አበባ ሲገሰግስ፤ የጣይቱ ሆቴል የላይኛው ክፍል የጥቁር አንበሳ ጦር መገናኛ ሬድዮ ተሰድሮበት የሚስጥር እና ግልጽ ግንኙነት ይደረግበት ነበር። ጃንሆይ ሚያዝያ 25 ቀን፣ 1928 የአዲስ አበባ ከተማን ለቀው ሲወጡ፤ ከተማውን ራስ አበበ አረጋይ በከንቲባነት ይቆጣጠሩት በነበረበትም ወቅት ጣይቱ ሆቴል ጊዜያዊ መገናኛቸው ነበር። ጃንሆይ አዲስ አበባን ለቀው እንደወጡ አመጽ ተቀሰቀሰ፤ ዘረፋም በረከተ። የክብር ዘበኞችም በንዴት ተነሳስተው አዲስ አበባ የሚገኙ አውሮፓውያንን ማሳደድ ጀመሩ። በዚህም ግዜ ጭምር… የብዙዎቹ መሸሻ ጣይቱ ሆቴል ነበር።
ጄነራል ፔድሮ ባዲዮ አዲስ አበባ ከገባ በኋላ፤ ከሰራዊቱ ጋር አብረው የመጡት የጣልያን ጋዜጠኞች እንዲያርፉ የተደረገው ጣይቱ ሆቴል ስለነበር፤ በተለይ አንደኛ ፎቅ ላይ የነበረው፤ ድሮ ሰራተኞች የሚተኙበት አሁን ጃዝ አምባ የተሰኘው ላውንጅ የሚገኝበት ቦታ… ጣልያኖቹ ጋዜጠኞች ለጋዜጣ ህትመት የሚሆኑ ፎቶ የሚያነሱበትና የሚያትሙበት ስፍራ ነበር። እንዲህ እንዲህ እያልን የጣይቱ ሆቴል ጥንታዊ ታሪኮችን መምዘዝ ከጀመርን ቦታ እና ግዜ አይበቃንም።
ሰዎች በጣይቱ ሆቴል የየራራሳቸው ትዝታ ይኖራቸዋል። ለምሳሌ እኔ ጣይቱ ሆቴልን ሳስብ፤ ቶሎ ወደ ህሊናዬ የሚመጣው የሙያ ወንድሜ እስክንድር ነጋ ነው። መጀመሪያ Habesha የተባለ እንግሊዛኛ ጋዜጣውን፤ ከዚያም ምኒልክ ጋዜጣን ማሳተም ከመጀመሩ በፊት ጣይቱ ሆቴል እየተገናኘን ሰፊ ውይይት እናደርግ ነበር። በተለይ ምኒልክ ጋዜጣን ከመጀመሩ በፊት ጣይቱ ሆቴል ከፊል ቢሯችን ሊሆን ምንም አልቀረውም። ምሽት ላይ ፒያሳ ከመሸብንም የጣይቱ ሆቴል መኝታ ቤቶች ቤቶቻችን ነበሩ። ይህ ሁሉ ታዲያ ሆቴሉ ተሽጦ ወደ ፍጹምዘአብ ከመዛወሩ በፊት ነው። ፍጹምዘአብ ጣይቱ ሆቴልን ከገዛው በኋላ ብዙም ወደዛ መሄዳችንን አላስታውስም። ስለዚህ “ድሮ እና ዘንድሮ” በማለት ለማወዳደር እንቸገራለን። ሆኖም በቅርቡ ብዙዎችን ያነጋገረው “አትሂድ” የሚለው የሜሮን ጌትነት ግጥም እና ሌሎች ስራዎች የተቀረጹት እዚሁ ጣይቱ ሆቴል፤ ጃዝ አምባ አዳራሽ ውስጥ ነበር። (ወጋችንን እናሳርግ)
በቅርቡ አገር ቤት ደርሶ ከተመለሰ ጓደኛዬ ጋር ስንጨዋወት ጣይቱ ሆቴል ሄዶ እንደነበር አወራኝ። በዚያው ስለሆቴሉ አያያዝ ጠየቅኩት። “ኢትዮጵያ ውስጥ የአጼ ምኒልክ፣ የእቴጌ ጣይቱ እና ሌሎች ታላላቅ ኢትዮጵያውያን ፎቶ በትልልቁ ተሰቅሎ ያየሁት ጣይቱ ሆቴል ውስጥ ብቻ ነው” አለኝ።
ስለጣይቱ ሆቴል ከናንተ ጋር ያወራነውን አወራን። ፍጹምዘአብ ብቸኛ ተጫራች ሆኖ ሆቴሉን እንዴት እንደገዛው፤ ታስሮ በነበረበት ወቅት ስለነበረው ሂደት… ብዙዎች ስለማያውቁት የፍጹምዘአብ የፕሬስ አስተዋጽኦ አወራን። ከዚህ ጨዋታችን በኋላ ግን ደጋግሜ የማስብ የነበረው … ‘በሙስናም ሆነ በጉብዝና ሆቴል አንድ ግዜ በፍጹምዘአብ ስር ወድቋል። ሌላ… ምኒልክን የሚጠላ፣ የኢትዮጵያ ታሪክን የሚያጥላላ ሰው ያንን ጥንታዊ ሆቴል ገዝቶት ቢሆን ኖሮ… ምናልባት ሆቴሉን አፍርሶ ወይም፣ ስሙን ቀይሮ ሌላ ነገር ቢያደርገው ማን ጠያቂ ነበረበት? ደግሞ ባለበትም ቢሆን ጥንታዊነቱን የለቀቀ ናይት ክለብ ወይም ልብስ ቤት ወይም ስጋ ቤት ወይም ሌላ ነገር ሊሆን ይችል አልነበረምን?’ እያልኩ ደጋግሜ እያሰብኩ፤ ፍጹምዘአብንም ከነጉድለቱ መልካም ስራውን እያሞገስኩ ሳለ የጣይቱ ሆቴልን መቃጠል እንደመርዶ እሁድ ማለዳ ላይ ሰማነ።
እናም ከዚህ ቃጠሎ ጀርባ፣ በወጋገኑ ውስጥ የምናየው ፍጹምዘአብ አስገዶም ወልደሚካኤልን በቁንጽል አስተዋወቅናቹህ። ጣይቱ ሆቴልን በብላሽም ይሁን በርካሽ ገዝቶት፤ ለግዜው የግል ንብረቱ ሆኗል። ከቃጠሎው በኋላ ከማንም ባላነሰ ሳይሆን በባሰ ሁኔታ ሊያዝን ይችላል… የሚል እምነት አለን። የሱም ሆነ የሁላችንም እንባ ሊደርቅ የሚችለው ግን… ጣይቱ ሆቴል ጥንታዊ መሰረቱን ሳይለቅ እንደገና ከገነባልን ነው። እናም ሁሌም በዝምታ ውስጥ ሆኖ ትልቅ ነገር ለሚያስበው ፍጹምዘአብም እንዲህ በሉልን። “የእያሪኮ ግንብ ስለሃጢያታቸው ብዛት በእሳት ወድሞ ቀረ። የምኒልክ እልፍኝ፣ የጣይቱ ማጀት ግን እንደገና አምሮ ይሰራ። እነሆ ዘንድ መሰረቱን ጣል – ምሰሶውንም ከፍ አድርግ። እነሆ ፀሃይቱም እንደወርቅ ጠልሰም ዳግም ትድመቅ! ”
አሜን! (አሳርገናል)

No comments:

Post a Comment