Saturday, January 10, 2015

ትንሽ ምስክርነት ስለ መረራ ጉዲና (ዶ/ር) (ቶፋ ቆሪቾ)


merera gudina j

ከመሰንበቻዉ መረራ ጉዲና ከ25 ዓመታት በላይ ካስተማረበት ዩኒቨርሲቲ ተባረረ የሚለዉ አስገራሚና አስደንጋጭ ወሬ ከተዛመተ በኋላ አነጋጋሪነቱ ሞቅ ብሏል፡፡ (በጨዋታችን ላይ የማከብረዉ መምህሬ ስለሆነ አንተ እያልኩ ነዉ የምጠራዉ … እሱም ቢሆን አንቱታዉን ብዙም የሚፈለገዉ አይደለም … አዉቃለሁ)፡፡ በይፋ ከዩኒቨርሲቲዉ መሰናበቱን የሚያስረዳ ደብዳቤ እንደረሰዉ ባይገልጥም ነገሩ እሳት ካየዉ … ነዉ እና የምናዝን እናዝናለን፡፡
ዶ/ር መረራን ሳዉቀዉ
ለመጀመሪያ ጊዜ መረራ የሚባል ኦሮሞ ኢትዮጵያዊ … በኢትዮጵያ ፖለቲካ ዉስጥ ጎልቶ መዉጣት የጀመረዉ ይመስለኛል በ1992 ብሔራዊ ምርጫ ወቅት ነዉ፡፡ በዚያን ጊዜ የደመቀ ባይሆንም ጥቂት ፖለቲከኞች ገዢዉን ፓርቲ ሲሞገቱ የሚያሳይ የቅድመ ምርጫ ክርክር በቴሌቪዥን ይለቀለቅ ነበር፡፡ ያኔ ታድያ የብዙዎችን ቀልብ የሳበዉ በእኩልነት የምንኖርባትን አዲሲቱን ኢትዮጵያን በጋራ እንመስርት የሚል ጎልቶ የሚሰማ የአንድ የፖለቲካ ሳይንስ ምሑር ድምፅ ነበር፡፡ … ለእኩልነት፣ ለጋራ መብት መከበር፣ ለመቻቻል፣ ለጋራ ብልፅግና፣ ለሰላም፣ ለመጪዉ ትዉልድ አስበን በጋራ እንስራ የሚለዉ ጥሪዉን ሲያስተላልፍ ይታወሰኛል፡፡ በተለይ ሰማያዊ ቀለም ያለዉ ሙሉ ጅንስ አለባበሱን አረሳዉም፡፡ በጋራ እንስራና እንተባበር በሚለዉ የዘወትር ጥሪዎቹ ይህ ፖለቲከኛ አሁንም በኢትዮጵያ ታሪክ ዉስጥ በጉልህ ታሪኩን መፃፍ ቀጥሏል፡፡
በቴሌቪዥን መስኮት የማዉቀዉን ሰዉ ለመጀመርያ ጊዜ በአካል ያገኘሁት 1995 የሁለተኛ ዓመት የዩኒቨርስቲ ትምህርቴን ለመቀጠል በፖለቲካል ሳይንስና ኢንተርናሽናል ሬሌሽንስ ዲፓርትመንት በገባሁበት ወቅት ነበር፡፡ በወቅቱ ፖለቲካል ገቨርናንስ የሚል የትምህርት ያስተምረን ነበር፡፡ አስታዉሳለሁ በርካቶቻችን ክፈለ-ጊዜዉን በናፍቆትና በጉጉት እንከታተል እንደነበር፡፡ ዶ/ር መረራ በሌሎች መድረኮች ላይ እንደሚያሳየዉ ተጨዋችነትና አዝናኝነት በክፍል ዉስጥም ኮሚክ ነገሮችን ይናገራል፡፡ በዚህ ዘዴዉ ትምህርቶቹን ተወዳጅ ከማደረጉም በላይ በቀላሉ ለመረዳትና ከነባራዊ ሁነቶች ጋር ለማገናዘብ እንዲቻል አድርጎ የማስተማር ብቃት እዳለዉ ብዙዎቻችን እንመሰክርለታለን፡፡ ከሁሉ የማረሳዉ በየንግግሮቹ መጨረሻ ላይ “Generally” የሚለዉን ሲሆን ሁሉ ነገር ጀነራሊ ከሆነ እንዴት ነዉ ነገሩ ብለን ብንጠይቀዉ እየሳቀ ልምድ እንደሆነበትና እየሳቀ አባባሉን ከቁም ነገር እንዳይወሰድ ያሳስበን ነበር፡፡
ዶ/ር መረራን በክፍል ዉስጥና ከክፍል ዉጪ ስናዉቀዉ የተለየ ሰዉ ነዉ፡፡ በሌላ አነጋገር በክፍል ዉስጥ ሲያስተመር ፍፁም ሊባል በሚችል ሁናቴ ሚዛናዊና ገለልተኛ አቛሞችን ነዉ የሚያንፀባርቀዉ፡፡ የፖለቲካ እምነቱን እና አመለካከቱን በግድ ልጋታችሁ የሚል ስብእና እንደሌለዉ ወዳጆቹ ብቻ ሳንሆን ኢህዴጋዊ አቛማቸዉን በይፋ የገለጡ ተማሪ ጓደኞቻችን ጭምር ነበሩ የሚመሰክሩለት፡፡ የሚገርመዉ በ1997 የምርጫ ዋዜማ እንኳን ነገሮች ተሟሙቀዉ በተለይ ዶ/ር መረራ ሕብረት የሚባለዉን ጥምር ፓርቲ እየመራ ከቅንጅት ጋር ኢሕዴግን እንደዚያ ሲያንጰረጵረዉ፤ ዉጪ ባለዉ አቋሙ እያወቅነዉ ክፍል ዉስጥ በጉዳዩ ላይ አሰተያየት ለመስጠት እኳንን አለመፈለጉ (ብዙዎቻችን ወቅታዊ ፖለቲካዉን የተመለከቱ ጥያቄዎች እናነሳለት ነበር) የቱን ያህል ሞያዉን የሚያከበርና በአካዳሚክ ነፃነት የሚያምን መሆኑን ለማሳየቱ እንመሰክር ነበር፡፡
ከ1997 ምርጫ ግርግር በኋላ ለድህረ ምረቃ ትምህርት ተመልሼ ሳገኘዉም በቅንነት ከማስተማር በቀር በክፍል ዉስጥ ፓርቲያዊ የሆኑ ነገሮችን ላለማንሳት ሲጠነቀቅ አዉቀዋለሁ፡፡ ዶ/ር መረራ ቢሮዉ ለሁሉም ተማሪዎች ከፍት የሆነ ሲሆን ማንኛዉንም ጉዳይ ይዞ ሄዶ ምክር ለመጠየቅ የሚመችና ቤተሰባዊ መንፍስ ያለዉ ሰዉ ነዉ፡፡ ከሌሎች የዲፓርትመንቱ መምህራን በተለየ መልኩ ቢሮ ዉስጥ ሲቀመጥ በሩን አይዘጋም፡፡ ስለሆነም ማንም ሰዉ ቢሄድ በቀላሉ ሊያገኘዉና ሊያወየዉ እንደሚችል አዉቃለሁ፡፡ በአጠቃለይ እንደ አብዛኞቹ የቀድሞ የዩኒቨርሲቲዉ መምህራን ፊዉዳላዊ አመለካከት የሌለዉ ሰዉን በመተባበር የሚያምን ሰዉ ነዉ፡፡
ከእዉቀት አንፃር ካየነዉ በፍጹም የሚታማም አይደለም፡፡ ከብዙዎቹ የላቀ ሁለገብ የሆነ ችሎታና እወቀት ያለዉ ሰዉ ነዉ፡፡ ሲያስተምር፣ የጥናት ፁፎችን ሲያማክር፣ ሞያዊ አስተያየቶችን ሲሰጥ፣ እንዲሁም በተለያዩ መድረኮች ንግግር ሲያደርግ አፍ የሚያሰከፍት አይነት ነዉ፡፡ የትምህርት ክፍሉ አሉት ከሚባሉ የጠለቀ እዉቀትና የማስተማር ችሎታ ካለቸዉ የአንድ እጅ ጣት የማይሞሉ መምሀራን ግንባር ቀደሙ ነዉ ቢባል ማጋነን አይሆንም፡፡
ማን ይጎዳል?
አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በብዙ መለኪያዎች ከነበረዉ ዝና፣ ክብርና ማእረግ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየወረደ መምታት ብቻ ሳይሆን እየዘቀጠ እደሆነ ይነገራል፡፡ ይህ ጉዳይ የሚታየዉ ከአጠቃለዩ ሃገራዊ የትምህርት ጥራት መጓደልና የደረጃ ማሽቆልቆል ጋር ብቻ መሆን የለበትም፡፡ ይልቁንም የዩኒቨርሲቲዉ ዛሬ ባለበት ደረጃ ላይ መገኘት እንደ አንድ ቀደምት ሃገራዊ ተቋም መፈራረስና ሁለነተናዊ ዉድቀት ነዉ፡፡ ያን የመሰለ ታሪካዊና በርካታ ምሁራንን ለሃገሪቱ ያፈራ ተቋም ዛሬ ላይ በአለም ከፍተኛ ዝና ካላቸዉ የትመህርት ተቋማት ጋር መወዳደር ሲገባዉ በአፍሪካ ዉስጥ ካሉት ዩኒቨርሲቲዎች ጋር ሲነፃፀር እዚህ ግባ የሚባል ቦታ የለዉም፡፡ ይኼ ጉዳይ በዩኒቨርሲቲዉ ዉስጥ ላለፍን ሁሉ አንግት የሚስደፋ ጉዳይ ሆኖ ይገኛል፡፡ ለምን ኢትዮጵያ የራሷ የሆነ ብራንድ አይኖራትም ብለን ለምንጠይቅ ምላሹ ምን ይሆን?
ከዩኒቨርሲቲዉ ዝቅ ብለን የፖለቲካ ሳይንስ እና ኢንተርናሽናል ሬለሺንስ (PSIR) የሚባለዉን የትምህርት ክፍል ያየን እንደሆነ የበለጠ የሚስደነግጥ ማሽቆልቆል ሂደት ዉስጥ እንዳለ ለመረዳት አያዳግትም፡፡ በርካታ እጋፋና ወጣት መምህራኖች በየጊዜዉ እየለቀቁ በመዉጣታቸዉ የትምህርት ክፍሉ በህንድ መምህራን እና አንዳንድ ነዉረኛ ሰዎች እንዲሞላ ተድረጓል፡፡ እዚህ ላይ የማስታዉሰዉ ከጥቂት ዓመታት በፊት የወቅቱ የዩኒቨርሲቲዉ ፕሬዘዳንት የነበሩት ፕሮፌሰር እንድርያስ እሸቴ ዘመድ እንደሆነ በፉከራ ይናገር የነበር ዶ/ር ኤርሚያስ አበበ (ያባቱን ስም ካሳትኩ ይቅርታ) የሚባል ሰዉ የድህረ-ምረቃ ተማሪዎችን ‘Foreign Policy and Diplomacy’ የሚል የትምህርት አይነት እንዲያስተምር ተመድቦ በርካታ የሚያሳፍሩ ተግባሮችን ሲፈፅም እንደነበር ምስክርነት ለመስጠት እችላለሁ፡፡ በስካር ጥንብዝ ብሎ በወሳንሳ በመጠጥ ቤት ጓደኞቹ ተደግፎ ከመምጣቱ በተጨማሪ በነዉረኛ ስድቦች ተማሪዎችን ይዘለፍ ነበር፡፡ የትምህርት ክፍሉ አሉት የሚባሉ ማምህራን ባለፉት ጥቂት ዓመታት ብቻ እንኳን ፍልሰት በሚመስል መልኩ በመልቀቃቸዉ የቱን ያህል የተዳከመ መሆኑን መገመት አያዳግትም፡፡
እናም የዶ/ር መረራና መሰል አንጋፋና ጠንካራ አመለካከት ያላቸዉ ምሁራን መልቀቅ የትምህርት ክፍሉን እና ዩኒቨርሲቲዉን ብቻ ሳይሆን በመላ ሃገሪቱ ላይ ሊደርስ የሚችለዉን ኪሳራ ማስላት አዳጋች አይሆንም፡፡

No comments:

Post a Comment