Monday, October 27, 2014

ወያኔ ሲያስር አሜን….ሲገድልም አሜን በኤፍሬም ማዴቦ October 8th, 2014


ብዕር የያዘ ማንም ሰዉ በዘመናችን ደግሞ የኮምፒተር መክተቢያ ፊቱ ላይ የደቀነ ሁሉ ከሱ ዉጭ ያለዉን ማንንም ሰዉ “ሌባ”፤ “ባንዳ” ወይም “ከሃዲ” እያለ እንዳሰኘዉ መጻፍ ይችላል። በተለይ በእንደኛ አይነቱ ሀላፊነትም ተጠያቂነትም በሌለበት ህብረተሰብ ዉስጥ ደግሞ የጓደኛዉ ሀሳብ ያልተስማማዉ ሁሉ እየተነሳ የገዛ ጓደኛዉን ባንዳና ከሃዲ አድርጎ ስለሚስለዉ የላይ የላዩን ብቻ ለሚመለከት ሰዉ አገራችን በባንዳና በአገር ወዳድ መሳ ለመሳ ለሁለት የተከፈለች ትመስላለች። እግዝአብሄር ይመሰገን እዉነቱ ግን ከዚህ እጅግ በጣም የተለየ ነዉ። ርዕሴን የጀመርኩት አሜን ብዬ ነዉና እስኪ አንባቢዉ አንተም አሜን በል። ባንዳነትና ከሃዲነት ኃብታምና በእድገት ወደፊት የገፉ አገሮችን እየዘለለ ደሃና ኋላ ቀር አገሮችን ብቻ የሚጠናወት ተራ በሽታ አይደለም። ብዙዎቻችን አምባገነን መሪዎቻችንን ሸሽተን የተጠለልንባት አገር አሜሪካ እነ ሄንሪ ቤስትንና ጆን ብራዉንን የመሳሰሉ ከሃዲዎችን እንዳበቀለች ሁሉ ኢትዮጵያችንም ትናንት እነ ኃ/ሥላሤ ጉግሳን ዛሬ ደግሞ የኃ/ሥላሤ ጉግሳ የልጅ ልጆች የሆኑትን እነ መለስ ዜናዊን፤ አባይ ፀሐዬንና ሰብሃት ነጋን የመሳሰሉ የለየላቸዉ ከሀዲዎችን አፍርታለች። በነገራችን ላይ ሙስሊሙ በዱአዉ፤ ክርስቲያኑ በፀሎት፤ ጠቢብ በጥበቡ ፤ፀሐፊ በምናቡ የባንዳዉንና የከሃዲዉን ብዛት ለመቀነስ ካልተባበሩ በቀር “ወላድ በድባብ ትሂድ” ብለን ባንመርቃቸዉም የባንዳ አባትና አናት አስካሉ ድረስ ባንዳም መወለዱ አይቀርም።
ደጅአዝማች ኃ/ሥላሤ ጉግሳ ማንም ሳያስገድደዉ ወድዶና ፈቅዶ ለወራሪዉ የጣሊያን ጦር ካደረ በኋላ ከጄኔራል ደቦኖ ጋር ሆኖ እናት አገሩን ኢትዮጵያን ወግቷል። ጣሊያኖች ኃ/ሥላሤ ጉግሳ ከነተከታዮቹ ከጎናቸዉ ተሰልፎ አገሩን ሲወጋ ያደረጉት የመጀመሪያዉ ነገር ይህ ከሃዲ ሰዉ ከጎናቸዉ መሰለፉን የሚያሳዩ ፎቶግራፎች ለዓለም ህዝብ ማሰራጨት ነበር። ታሪክ እራሱን ይደግማል ሲባል አይኑ አላይ እያለዉ በጆሮዉ ብቻ ለሰማ ሰዉ ዛሬ ማረጋገጫዉ እነሆ በግልጽ ቀርቦለታል። ትናንት ማክሰኞ መሰከረም 27 ቀን የወያኔ ቴሌቭዥንና ሬድዮ ኢትዮጵያ ዉስጥ በጋዜጠኞች ላይ የሚፈፀመዉን እስርና ስደት፤ ወያኔ በወገኖቻቸን ላይ የሚፈጽመዉን የዕለት ከዕለት ሰቆቃና እንዲሁም በቅርቡ አምቦና ኦጋዴን ዉስጥ የተካሄዱትን የጅምላ ግድያዎች የሚደግፉ የዚህ ዘመን ኃ/ሥላሤ ጉግሳዎች ዋሺንግተን ዲሲ ዉስጥ ያካሄዱትን የክህደት ሰለማዊ ሠልፍ በተደጋጋሚ ለህዝብ አቅርበዋል። እነዚህ ትናንት ክቡር ባንዲራችን በአለባሌ ሰዉ አንደበት “ጨርቅ” ተብላ ስትሰደብ ከተሳዳቢዉ ሰዉ ጎን ቆመዉ የሳቁና የተሳለቁ ከሃዲ ሆድ አምላኪዎች ዛሬ “ባንዲራችን ተደፈረ” ብለዉ የአዞ እምባ ያነቡብናል። የትኛዉ ባንዲራ? ለመሆኑ እነዚህ “እናቴን ያገባ ሁሉ አባቴ ነዉ” ባዮች ጀግናዉ ዘርዐይ ደረስ ጣሊያኖችን በራሳቸዉ አደባባዮች አንገታቸዉን በጎራዴ የቀላዉ ለዬትኛዉ ባንዲራ እንደሆነ ያዉቃሉ? እነ አብዲሳ አጋ፤ በላይ ዘለቀ፤ ባልቻ አባ ነብሶና እልፍ አዕላፋት የኢትዮጵያ ልጆች ምትክ የሌላትን ህይወታቸዉን የሰጡት ለዬትኛዉ ባንዲራ አንደሆነ ያዉቃሉ?
እነዚህ ወያኔ አዲስ አበባ ዉስጥ የገዛ ወገኖቻዉን ሲያስርና ሲገድል አሜን ብለዉ ዋሺንግተን ዲሲ ዉስጥ ሠላማዊ ሠልፍ የሚወጡ የለየላቸዉ ከሃዲዎች ባንዲራ አዲስ መንግስት በመጣ ቁጥር እንደ ፖሊሲና እንደ ካቢኔ ሚኒስቴር የማይቀያየር ቋሚ የአገር ማንነትና የትዉልድ ትስስር መታወቂያ መሆኑን ሊገነዙ ይገባል። ባንዲራ ምክንያታዊ በሆነ መልኩ ሊቀየር ይችላል ብለን ብናስብ እንኳን ምን አይነት ሰዎች ብንሆን ነዉ ባንዲራን የመሰለ ህዝብና አገር ማስተሳሰሪያ ማተብ ኢትዮጵያንና ታሪኳን ከልቡ ለሚጠላዉ መለስ ዜናዊና የትግራይ ሪፓብሊክ ካላቋቋምኩ ብሎ ይታገል ለነበረዉ ለከሃዲዉ ስብሀት ነጋ የምንተዉላቸዉ? ደግሞም እነዚህ ምናምንቴዎች አንደሚሉት ባንዲራችን ላይ ባዕድ አካል ሆኖ የተለጠፈዉና የኢትዮጵያ ህዝብ በተለምዶ “ባላ አምባሻዉ” እያለ የሚጠራዉ የወያኔ ጨርቅ እዉነትም ኢትዮጵያ ዉስጥ የብሄር ብሄረሰቦችን እኩልነት አረጋግጦ ቢሆን ኖሮ ዛሬ አገራችን በየቀኑ ብሄር ብሄረሰቦች ዉጣልኝ አልወጣም እየተባባሉ የሚተላለቁባት አገር አትሆንም ነበር። አባቶቻችን የሞቱት ለአረንጓዴ፤ ብጫና ቀይ ባንዲራ ነዉ፤ እኛም ዛሬ በየተሰደድንበት አገር አገሬን እያሰኘ የሚያስጮኸን ይሄዉ አረንጓዴ፤ ብጫ ቀይ ባንዲራችን ነዉ። አገር ቤት ያለዉ ኢትዮጵያዊም አንዱን “ባላአምባሻዉ” ሌላዉን ደግሞ ባንድራዬ እያለ የሚጠራዉ ይህንኑ አረንጓዴ፤ ብጫና ቀይ ባንዲራዉን ነዉ። በአንዲት አገራችን ኢትዮጵያ ዉስጥ እነሱም እኛም ለየቅላችን የኛ የምንለዉ ባንዲራ ሊኖር በፍጹም አይችልም። ይልቅ ወያኔዎች ሲጠፉ እነሱ ይዘዉብን የመጡት ኮተቶ ሁሉ አብሯቸዉ መጥፋቱ አይቀርምና ዛሬ “ባንዲራችን ተደፈረ” ብላችሁ የምታቅራሩ እዉሮች ነገ ከወያኔ በጸዳችዉ ኢትዮጵያ ዉስጥ ጭራሽ ባንዲራ ላይኖራችሁ ይችላልና መጀመሪያ ከራሳችሁ ጋር ቀጥሎም ከአገራችሁ ከኢትዮጵያ ጋር እንድትታረቁ አጥብቄ እማጸናችኋለሁ።
የወያኔን ቂልነትና ባዶነት በሰብኩ ቁጥር ትዝ የምትለኝ አንዲት ቀልድ ብጤ አለችና እስኪ ለፈገግታ ትሆናለችና አዳምጡኝ። ሁለት አመት የፈጀዉ የኤርትራና የኢትዮጵያ አላስፈላጊ ጦርነት እንዳለቀ በጦርነቱ ወቅት ስንቅና ትጥቅ በማመላለስ ትልቅ ዉለታ የዋለች ኣንዲት አህያ ጦርነቱ አብቅቶ የድል በዐል ሲከበር መስቀል አደባባይ ተጋብዛ መለስ ዜናዊ ፊት ትቀርባለች፤ በቋንቋ ይግባቡ ነበርና መለስ ጎንበስ ብሎ በጆሮዋ አንድ ነገር ሹክ ሲላት አህይት በደስታ እየፈነጠዘች አደባባዩን መዞር ጀመረች። በልማታዊ አህይት ዝላይና ፍንጠዛ ግራ የተጋቡት የወያኔ ጋዜጠኞች ዜና ያገኙ መስሏቸዉ “ታላቁ መሪ” ምን አለሽ ብለዉ አህይትን ጠየቋት። የዕድሜ ልክ የህወሓት አባል ሆነሻል ተብያለሁ ብላ አህይት ዝላይዋንና ፍንጠዛዋን ቀጠለች።
ትናንት እዚህ ዋሺንግተን ዲሲ ዉስጥ የወያኔን ጭፍጨፋ፤ እስርና በዘር መድሎ የተጨማለቀ ስርዐት አበጀህ ቀጥልበት ብለዉ አደባባይ የወጡ ጥቂት ህሊና ቢሶችና እነሱን አመስግኖ የነጻነት አርበኞችን “ዱሪዬዎች” ብሎ የዘለፈዉ የአድር ባዮች ሁሉ አድርባይ የሆነዉ ግርማ ብሩ ከዚያች ባድመ ላይ ብዙ ስንቅና ትጥቅ ካመላለሰችዉ ጎበዝ አህያ የሚለዩበት መንገድ ቢኖር አህያዋ ማሰብ ስለማትችል አለማሰቧ እነሱ ግን ማሰብ እየቻሉ አለማሰባቸዉ ብቻ ነዉ። በተረፈ እነሱም አህያዋም የወያኔ አባልነታቸዉ ያስደስታቸዋል፤ ምክንያቱም ሁለቱም አያስቡም። መቼም የገዛ ወንድሙና እህቱ ሲታሰሩ፤ ሲደበደቡና ሲገደሉ አሜን ብሎ ተቀብሎ ነብሰ ገዳዮችን ደግፎ ሰላማዊ ሠልፍ የሚሰለፍ የሰዉ ዘር ያለዉ ኢትዮጵያ ዉስጥ ብቻ መሆን አለበት። ለዚያዉም በወያኔ ዘመን ብቻ!
እነዚህን ሆዳሞች ደግሜ ደጋግሜ እዉሮች እያልኩ የምጠራቸዉ አለምክንያት አይደለም። በእርግጥም ስለማያዩ ነዉ። ባለፈዉ ወር አዚህ አሜሪካ ሚዙሪ ግዛት ፈርግሰን የሚባል ከተማ ዉስጥ ከባድ መሳሪያ የታጠቁ ፖሊሶች መሳሪያቸዉን ሰላማዊ ሰልፈኛዉ ላይ ስላዞሩ (ልብ በሉ ስላዞሩ ነዉ ያልኩት እንጂ ስለተኮሱ አላለኩም እነሱም አላደረጉትም) የአሜሪካ ህዝብ፤ መሪዎችና የህዝብ ተወካዮች ምን ያህል እንደተንጫጩ ሁላችንም ተመልክተናል። እነዚያ እዉሮች ያልኳቸዉ ወንድሞቻችንም እኛ የተመለከትነዉን ተመልክተዉት ይሆናል፤ ግን እነሱ የአዕምሮ እዉራን ናቸዉና ስዕሉን ብቻ ነዉ እንጂ ቁም ነገሩን አላዩትም። ስለዚህም ነዉ የነሱ ድፕሎማት ተብዬዉ ድንጋይ ራስ (ርዕስ እምኒ) አዲስ አበባ ዉስጥ ያለ መስሎት ሠላማዊ ሠልፈኛ ለመግደል ደጋግሞ ሲተኩስ አበጀህ ብለዉ ሠላማዊ ሠልፍ የወጡለት። እግዚአብሄር ከዚህ አይነቱ የአዕምሮ እዉርነት ያድነን! እባካችሁ አሁንም አሜን በሉ። እኔ እያረረ የሚስቅ ማሽላ ብቻ ይመስለኝ ነበር . . . . ለካስ የገዛ ወገኖቹ ሲገደሉ ደስ ብሎት የሚስቅ ሰዉም አለ። አቤት እግዚኦ!!!!
ሌላዉ የገረመኝ ነገር ቢኖር እነዚህ የአዕምሮ እዉራን ትናንት ረፋዱ ላይ ለአሜሪካዉ ዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጆን ኬሪ በጻፉት ደብዳቤ ግንቦት 7 ያ እንቅልፋም ፓርላማቸዉ “ሽብርተኛ” ብሎ የፈረጀዉ ድርጀት ነዉና ምነዉ ዝም ብላችሁ ታያላችሁ ብለዉ ኬሪን መወትወታቸዉ ነዉ። ኬሪ እንደነሱ ጨካኝና አምባገነን መሪዎች የማይወደዉንና የሚጠላዉን ሁሉ አይንህ አላማረኝም እያለ ማሰር የሚችል መስሏቸዋል። እነዚህ ሆዳቸዉ ልባቸዉን የሸፈነ ከሃዲዎች አይገባቸዉም አንጂ የነሱን “ግንቦት ሰባቶችን” እሰሩልን ብሎ ጥያቄ እንኳን ኬሪ የአለማችን ሀይለኛዉ መሪ አባማም ማስተናገድ አይችልም። እኛስ ብንሆን የምንታገላቸዉ ለዚሁ ነዉኮ – ኢትዮጵያን የሚመራ ሁሉ ሀሳባችን ከሀሳቡ በተጋጨ ቁጥር አንዳያስረንና እንዳይደገድለን። እኔኮ ምን ይሻለኛል . . . . በአንድ በኩል ኢትዮጵያዉያን የወገኖቻቸዉን መገደል ተቃዉመዉ ሠላማዊ ሠልፍ ሲወጡ የወያኔዉ ተላላኪ ግርማ ብሩ የኤርትራን መንግስት ይከስሳል፤ የአይጥ ምስክር ድንቢጥ እንዲሉ የግርማ ብሩ ተላላኪዎች ደግሞ (የተላላኪ ተላላኪ ማለት ነዉ) ግንቦት ሰባት የሚረዳዉ በኤርትራ መንግስት ነዉና ስጋታችንን እዩልን እያሉ ኬሪን ይለማመጡታል። መቼም አዉቆ የተኛን ቢቀሰቅሱት አይነቃም ነዉና የወያኔ ደጋፊዎች አይገባቸዉም አንጂ ለሻዕቢያ ጎንበስ ቀና እያሉና የሻዕቢያን መሪዎች እንደ ታቦት እየተሳለሙ ለዚህ ዛሬ ላሉበት ደረጃ የበቁት የወያኔ መሪዎች ናቸዉኮ። ዛሬ በባነኑ ቁጥር አንዴ ግንቦት ሰባት አንዴ ሻዕቢያ እያሉ ዛር እንደያዘዉ ሰዉ የሚያጓሩትም ተደምስሰዉ ከታሪክ ምዕራፍ የሚፋቁት በዚሁ እንደ ህጻን ልጅ እጃቸዉን ይዞ ለታሪክ ባበቃቸዉ በሻዕቢያ በኩል መሆኑን በሚገባ ስለሚያዉቁት ብቻ ነዉ። ምድረ የወያኔ አጎብጋቢዎች ዛሬ እቅጩን ልንገራችሁ፤ ወደዳችሁም ጠላችሁ ይህ “ልማታዊ” ብላችሁ የምትጠሩት ነብሰ ገዳይ አገዛዝ ይደመሰሳል- ስጋታችሁ ትክክለኛ ስጋት ነዉ። ግን ከዚህ ስጋት የሚያድናችሁ ኬሪ ሳይሆን የራሳችሁ ሂሊና ብቻ ነዉና ሳይዉል ሳያድር ዛሬዉኑ ኑና ከህዝብ ጎን ተሰለፉ፤ አለዚያ ዕድላችሁ ከኑግ የተገኘህ ሰሊጥ አብረህ ተወቀጥ ይሆናል። መቼም እንደኔዉ የዚያች ምስኪን አገር ልጆች ናችሁና በተረት ብነግራችሁ ይገባችኋል ብዬ ነዉ እንጂ በእናንተና መወቀጥ በሚገባዉ ኑግ መካከል ምንም ልዩነት የለም።
የዘረኞቹ የወያኔ መሪዎችና እንደ ችግኝ ኮትኩተዉ ያሳደጓቸዉ ቡችሎቻቸዉ አስቂኝ ታሪክ በዚህ ብቻ አያበቃም፤ እነዚህ ጣምራ ጉደኞች ብዙ ተነግሮ የማያልቅ ጉድ አላቸዉ። ወያኔዎች ጋዜጠኛ እያሰሩና ከአገር እንዲሰደድ እያደረጉ ተዉ ያላቸዉን ፀረ አገርና ፀረ ልማት ይሉታል፤ በየሰላማዊ ሠልፉ ላይ ንጹህ ዜጎችን በጅምላ ሲጨፈጭፉ ምነዉ ያላቸዉን ደግሞ ሽብርተኛ ብለዉ ያስሩታል። እነዚህ አረመኔዎች ይህንን የመሰለ ለጆሮ የሚቀፍ ወንጀል በህዝብና በአገር ላይ ፈጽመዉ ሰዎች በነጻነት ወደሚኖሩበት አገር ሰዉ መስለዉ ሲመጡና ስንቃወማቸዉ ደግሞ እዚህ ዉጭ አገር ያስቀመጧቸዉ ተናካሽ ዉሾቻቸዉ “ኢትዮጵያዊ ጨዋነት” የጎደላቸዉ ብለዉ ይዘልፉናል። ለመሆኑ ለእነዚህ እንደ ዉሻ ቁራሽ ስጋ በተወረወረላቸዉ ቁጥር ለሚያላዝኑ ምናምንቴዎች ማነዉ ኢትዮጵያዊ ጨዋነት እንደነሱ ነዉርን አሜን ብሎ መቀበል ብሎ የነገራቸዉ? ዜጎችን አንደ እንስሳ አየጎተቱ ገድለዉ አስከሬኑን በሟቹ ወንድም እያስጎቱና ይህንን ነዉር በቪድዮ እየቀረጹ መሳቅና መሳለቅ ነዉ ኢትዮጵያዊ ጨዋነት ወይስ ይህንን ኔሮና ሂትለር ምን አደረጉ የሚያሰኝ ጭካኔና አረመኔነት መቃወም ነዉ ኢትዮጵያዊ ጨዋነት? አዲስ አበባ ዉስጥና እዚህ ዋሺንግተን ዲሲ ዉስጥ ተቃዋሚ ኃይሎችን “ኢትዮጵያዊ ጨዋነት” የጎደላቸዉ ብለዉ የዘለፉት ሬድዋን ሁሴንና ግርማ ብሩ የዉኃ ጠብታን ያክል ኢትዮጵያዊ ጨዋነት በደማቸዉ ዉስጥ ቢኖር ኖሮ “ኢትዮጵያዊ ጨዋነት” የኢትዮጵያዉያንን ህይወት በየአደባባዩ መቀማት አይደለምና እናከብራቸዉ ነበር እንጂ በወጡና በገቡ ቁጥር ስማቸዉን እየጠራን ሌባና ከሃዲ እያልን አናሸማቅቃቸዉም ነበር። ኢትዮጵያዊ ጨዋነት ስንታሰርና ስንዋረድ እልል፤ ስንገደል ደግሞ አሜን ብለን እንደ በሬ አንገታችንን ለቢለዋ መስጠት ማለት አይደለም። ኢትዮጵያዊ ጨዋነት ለወገን ማዘን ነዉ፤ ኢትዮጵያዊ ጨዋነት ወገን ሲጎዳና ሲጠቃ ከለላ መሆን ነዉ። ከሁሉም በላይ ደግሞ ኢትዮጵያዊ ጨዋነት ዜጎች ሰቆቃ ሲፈጸምባቸዉና ሲገደሉ ቆሞ ከመመልከት ይልቅ ወይም የገዳዮች ጠበቃ ከመሆን ባጭር ታጥቆ ነብሰ ገዳዮችንና የጭካኔ ምልክቶችን ከአገር አናትና ከህዝብ ጀርባ ላይ ማስወገድ ነዉ – ወላድ በድባብ ትሂድ – ይህንን የሚያደርጉ የቁርጥ ቀን ልጆች እናት ኢትዮጵያ ትናንንት ነበሯት፤ ዛሬ አሏት ነገም ይኖሯታል።

1 comment:

  1. Casino Game For Sale by Hoyle - Filmfile Europe
    ventureberg.com/ casino-games งานออนไลน์ › casino-games 토토 사이트 › casino-games › casino-games Casino Game for herzamanindir sale by Hoyle on Filmfile Europe. Free shipping for most countries, no download sol.edu.kg required. Check the deals we have.

    ReplyDelete