Monday, June 23, 2014

የ2007 የመንግሰት በጀት ሚስጥር

ከግርማ ሰይፉ ማሩ


የኢትዮጵያ በጀት በደንብ አድርጎ ለመረመረው ሀገሪቱ ያለችበትን ፖለቲካ ሁኔታ የሚያሳይ ነው፡፡ ይህም ማለት በበጀቱ ውስጥ የቻይና፣ ምዕራባዊያን ሀገሮች እንዲሁም የምዕራብ ሀገሮች ይዞታ የሚባሉት አለም አቀፍ ባንኮች እጅ በግልፅ የሚታይ ነው፡፡ እንደምታውቁት መንግሰት ለ2007 ዓመተ ምህረት ያቀረበው በጀት ብር 178.6 ቢሊዮን ነው፡፡ ዘጠኝ ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር አካባቢ ማለት ነው፡፡ መደበኛው ወጪ እና የክልሎች ድጋፍ ሙሉ በሙሉ በሀገር ውስጥ የሚሸፈን ሲሆን ዋና ዋና የካፒታል በጀት ደግሞ ከመደበኛ ወጪ እና ክልሎች ድጋፍ ከሚተርፈው አነሰተኛ የሀገር ውስጥ ገቢ እና ለበጀት ጉድለት ለመሸፈን ከታሰበው ከሀገር ውስጥ ባንኮች ብድር ይሸፈናል ተብሎ የሚጠበቅ ነው፡፡ ከአጠቃላይ በጀቱ 19.2 በመቶ ከእርዳታና ብድር ይሸፈናል በዝርዝር ሲታይ ግን የመደበኛ በጀቱ 21.8 ከመቶ፣ የካፒታል በጀቱ ደግሞ 36.5 ከመቶ የሚሸፈነው ከብድርና እርዳታ ነው፡፡

ስንት ሰው እንደሚያስታውስ ባላውቅም የቀድሞ አዲስ ጉዳይ ጋዜጣ (ሁሌም ጋዜጣ ሳስብ የሚናፍቀኝ) በአንድ ወቅት የቀረበን በጀት ይህ በጀት ኢትዮጵያዊ በጀት ነው ወይ? የሚል ጥያቄ አንሰቶ ነበር፡፡ የበጀትን ዜግነት የጠየቀበት ገፊ ምክንያት በዚያን ሰሞን መወያያ፤ በአሁኑ ጊዜ ጠርናፊ ህግ የሆነውን የሲቪል ማህበራት ህግ ነበር፡፡ ይህ አፋኝ ህግ ማነኛውም በኢትዮጵያ ውስጥ የሚንቀሳቀስ ሰቪል ማህበር በጀቱ ከአስር በመቶ በላይ ከውጭ ከሆነ ኢትዮጵያዊ አይደለም ነው የሚለው፡፡ አሁን በሀገራችን የሚንቀሳቀሱት ብዙዎች መንግሰታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የተመዘገቡት በኢትዮጵያዊነት ሳይሆን “ረዚደንት” በሚል ቅፅል ነው፡፡ አዲስ ጉዳይ ጋዜጣ ይህን በጠየቀበት ወቅት የሀገሪቱ በጀት ከ40 በመቶ በላይ ከውጭ እርዳታ ሰለነበር ይህ መንግሰት ይህን ያህል ከውጭ የሚያገኝ ከሆነ ኢትዮጵያዊ አይደለም የሚል መከራከሪያ ይዞ ወጥቶ ነበር፡፡ ይህን ሰፋ አድርገው በመተርጎም አንድ አንድ ሰዎች የገቢ ምንጭ ዜግነት የሚወስን ከሆነ ብዙ ኢትዮጵያዊያን ከውጭ ከሚኖሩ ዘመዶቻቸው በሚላክላቸው ገንዘብ የሚተዳደሩ ስለሆነ ዜግነታቸው ኢትዮጵያዊ መሆን የለበትም ብለው ነበር፡፡ ስላቅ መሆኑ ነው፡፡ ያለበለዚያ ደግሞ የሚልኩላቸው ዘመዶቻቸው ዜግነት ያልቀየሩ በመኖሪያ ፍቃድ (ረዚደንት) የሚኖሩ መሆናቸውን ማረጋገጥ ይጠበቅባቸዋል፡፡

የሰዎችን ወይም የድርጅቶችን ዜግነት ኢትዮጵያዊ ወይም የውጭ ለማድረግ የገቢ ምንጭ መስፈርት መሆን የለበትም የሚለውን መከራከሪያ መንግሰት በዋዛ ያለፈው እንዳይመስላችሁ፡፡ መፍትሔ ብሎ የያዘው በተቻለ መጠን መንግሰት በጀቱን በመከፋፈል እና የተወሰኑት ወደ ጎን በማድረግ የብድርና የእርዳታ ገንዘቡ እንዳይታይ ማድረግ ነው፡፡ ለዚህም ነው መንግሰት ከፍተኛ መዋለ ንዋይ ከሚፈስባቸው የመሰረተ ልማቶች ውስጥ ዋና ዋና የሆኑትን ለምሳሌ እነ ቴሌ፣ መብራት ሀይል፣ ባቡር፣ የመሳሰሉት በሪፖርት ውሰጥ በስፋት እንደሰኬት ተካተው በበጀት ውስጥ ግን አይታዩም፡፡ ሉሎች ፋብሪካዎች ለምሳሌ ስኳር ፋብሪካ፣ ማዳበሪያ ፋብሪካ የመሳሰሉት ትልልቅ የመንግሰት ፕሮጀክቶቸ በበጀት ውስጥ የሉም፡፡ እነዚህ ከፍተኛ መዋለ ንዋይ የፈሰሰላቸው የመንግሰት ኢንቨስትመንቶች ከበጀት ውሰጥ እንዲወጡ የተደረጉት ደግሞ ብዙዎች በብድር የሚሰሩ ናቸው፡፡ የእነዚህ ፕሮጀክቶች የብድር ሂሣብ በበጀት ውስጥ ቢደመር የመንግሰትን በጀት ዜግነቱ ኢትዮጵያዊ ላይሆን ነው ማለት ነው፡፡ ለነገሩ በሲቪል ማህህበራት ትርጉም እነዚህ ሁሉ ተቀንሰው አሁን የቀረበው የመነግሰት በጀት ኢትዮጵያዊ በሚያደርገው ደረጃ ላይ አይለም፡፡ ምክንያቱም ከአጠቃላይ በጀቱ 19.2 በመቶ ከውጭ ብድርና እርዳታ የሚገኝ ስለሆነ ማለት ነው፡፡

መንግስት በበጀት ውስጥ ያካተታቸው በእርዳታና ብድር የተገኙ አብዘኞቹ የካፒታል ወጪዎች ለኤኮኖሚ ሴክተር መንገድ፣ ግብርና እና ውሃ ሲሆን፤ እርዳታው ደግሞ ለጤናው ሴክተር የተመደበ ነው፡፡ የእነዚህ ገንዘቦች ዋናኛ ምንጮች ደግሞ የኒዎ ሊብራል አራማጆች የሚባሉት መንግሰታት እና የእነዚሁ መንግሰታት ይዞታ ናቸው የሚባሉት ባንኮች የሰጧቸው ብድሮች ናቸው፡፡ እነዚህ መንግሰታት እና በቁጥጥራቸው ስር ያሉት የፋይናንስ ተቋማት ኢትዮጵያዊያን ጤናቸው እንዲጠበቅ የተሻለ መንገድ እንዲኖረን፣ ምርታማ ግብርና እንዲሁም ንፁህ ውሃ እንዲኖረን ዕርዳታና ብድር እየሰጡን፤ በሌላ በኩል ደግሞ ብጥብጥ እንዲነሳ የቀለም አብዮት ይደግፋሉ ብሎ ስጋት ውስጥ መውደቅ አይቃረንም ወይ? ይህ በእውነት የአብዮታዊ ዲሚክራሲ ወይም የልማታዊ መንግሰት ቅዠት ይመስለኛል፡፡

በጣም የሚያስገርመው ደግሞ በዋነኝነት ከፍተኛ እርዳታ የሚሰጡን መንግሰታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች በኩል አድርገው በቀለም አብዮት ሊያጠፉን ነው የሚባሉት የኒዎ ሊብራል አራማጅ ተብለው የተፈረጁት ሀገሮች መንግሰታት ናቸው፡፡ ከነዚህ ውሰጥ ቻይና እንደ መንግስት የምትሰጠን እርዳታ በሀገር ውስጥ ከውጭ ሀገር ዜጎች ምዝገባና የስራ ፈቃደ ከምናገኛው ያንሳል፡፡ ከሌሎቹ ሀገራት ጋር ሲነፃፀር ደግሞ ከአንድ መቶኛ ያነሰ ነው፡፡ ቻይና ሀገራችን በበጀት ውስጥ ከተካተተው ብድር ከ59 በመቶ በላይ ሰጥታናለች፡፡ ይህ ቻይና የሰጠችን ብድር ብዙ ስለሆነ ሳይሆን መንግሰታት ለኢትዮጵያ የሰጡት ብድር እጅግ ዝቅተኛ ከመሆኑ የመጣ ከፍተኛ የመቶኛ ድርሻ ነው፡፡ ቻይና በጀት ውስጥ ባልገባው ብድር ከፍተኛ አበዳሪያችን ነች፡፡ የቻይና ብድር በዋነኝነት በበጀት ውስጥ ባለተካተቱት ከፍተኛ የመንግሰት የመሰረተ ልማቶች እና የኤኮኖሚ ሴክተሮች ላይ ነው፡፡ ለምሳሌ ከበጀት እንዲወጣ የተደረገውን የቴሌን ማስፋፊያ ብቻ ብንወሰድ ወደ 32 ቢሊዮን ብር ወይም 1.6 ቢሊዮን በላይ የአሜሪካን ዶላር በ2007 በጀት ተብሎ የተያዘውን 18 ከመቶ ይሆናል፡፡ ይህ ገንዘብ በጀት ውስጥ ቢታይ እና የመንግሰትን የዜግነት መስፈርት ብንጠቀም መንግሰት ኢትዮጵያዊ ነው ለማለት ይቻላል ወይ? በጀት የመንግሰትን አቅም የሚያሳይ መለኪያ ነው በሚለው ልማዳዊ መለኪያ ለመጠቀም ለሚፈልግ ለቀጣይ ዓመት የቀረበው በጀት ትክክለኛውን የመንግስት ጡንቻ የሚያሳይ ነው ብለን ለመውሰድ እንቸገራለን፡፡

የኢኮኖሚና ፋይናንስ ሚኒሰትሩ አቶ ሶፊያ አህመድ በዚህ ጉዳይ በተደጋጋሚ በግንባር ቀደምነት የሚያነሱት የኢትዮጵያ አየር መንገድን ነው፡፡ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በዕዝ ኢኮኖሚ በሚባለው በደርግም ጊዜ ቢሆን ሪፖርቱን በይፋ ያቀርባል አቶ ሶፊያ ግን ይህን እንዲያደርግ ያለበትን ዓለማ አቀፋዊ ጫና የምንረዳ አይመስላቸውም፡፡ ያለበለዚያ ቦይንግ መግዣ ገንዘብ ሊገኝ እንደማይችል ግልፅ ነው፡፡ አሁን እኛ የግልፅነት ችግር አለባቸው እያልን ያለነው የብረታ ብረትና ኢንጂነሪን የሚባለው አስማተኛ ድርጅት የሚሰራው ሰራ የሚያገኘው ገቢና ወጪው በግልፅ አይታወቅም ነው፡፡ እጅግ ብዙ ሀብት ፈሶበትም የሚያመጣው ትርፍ ተመጣጣኝ አይደለም እያልን ነው፡፡ በቅርቡ ከመንግሰት ድርጅቶች ይገዛው የነበረውን የወዳደቁ ብረቶች ግዢ እንዲያቆም መታዘዙ ይታወቃል፡፡ ለምን? የፀረ ሙስና እና ሰነምግባር ኮሚሸን እነዚህ ተቋማት ለምዝበራ እንደሆነ ሪፖርት አቅርቧል፡፡ ለነገሩ ይህ ድርጅት ተጠሪነቱም ለመንግሰት የልማት ድርጅት አይደለም፡፡ ሌሎቹም ኮርፖሬሽኖች ለምሳሌ የሰኳር ኮርፖሬሽን ስር ነው የሚባለው ተንዳሆ የሰኳር ፕሮጀክት ያለበትን ጉድ የማያውቅ ያለ አይመስለኝም፡፡ በጀት ውስጥ የገባውን የመከላከያ በጀት ስንመለከት ደግሞ በየሳምንቱ እሁድ በሚያቀርበው የቴሌቪዥን ፕሮግራ በነፃ ገበያ ሰርዓት እየተወዳደረ መነገዱን ቢነግረንም፡፡ በግልፅና በሰውር የሚሰራቸው የገቢ ማስገኛ ገንዘቦች እንዳሉት እየታወቀ ከውስጥ ገቢ የሚባል አንድም የገቢ ርዕስ በጀቱ ላይ አይታይም፡፡ ስለዚህ የኢትዮጵያ የመከላከያ በጀት ይህ ብቻ ነው ብሎ ለመውሰድ አይቻልም፡፡ የመንግሰት ጡንቻ በመከላከያ በኩል ከዚህ እንደሚበልጥ ለማወቅ ደግሞ ልዩ እውቀት አይጠይቅም፡፡ ለዚህ ነው የመንግሰትን ትክክለኛ ቁመና የሚያሳይ በጀት አይደለም የምንለው፡፡

እነዚህ እርዳታ እየሰጡን ብድር የማይሰጡን መንግሰታት ምክንያታቸው ምንድነው? ብሎ መጠየቅም ተገቢ ይመሰለኛል፡፡ በኒዮሊብራል አሰተሳሰብ ተፈርጀው ሀገራችን ላይ የቀለም አብዮት ሊያመጡ ያሴራሉ የሚባሉት ሀገራት በዋና ዋና የንግድ እና ኢንቨስትምነት ውስጥ እጃቸውን ለማስገባት ወደኋላ ያሉት ለምንድነው? በተቃራኒው ደግሞ ቻይና በእነዚህ ወሳኝ የኤኮኖሚና የንግድ ኢንቨስትመንት ውስጥ እጇን በሰፊው የምትዘረጋው ለምንድነው? ብሎ መጠየቅ እና መልስ መሻት ግድ ይላል፡፡ በእኔ እምነት የምዕራባዊያን መንግሰታት በኢትዮጵያ ውስጥ ባሉ የኢኮኖሚ መስኮች ውስጥ ለመሳተፍ ውሳኔ የሚሰጡት መንግሰታት ሳይሆኑ በየሀገሮቻቸው ያሉት የግል ባለሀብቶች ናቸው፡፡ የመንግሰታት ድርሻ ለባለሀብቶች ትክክለኛ መረጃ እንዲደርሳቸው ማድረግ እና ተገቢውን ከለላ መስጠት ነው፡፡ የግል ባለሀብቶች ደግሞ መረጃ የሚያገኙት ከኢቲቪ አይደለም፡፡ ለያየ መልኩ በሀገራችን ያለውን ሁኔታ አብጠርጥረው ያውቁታል፡፡ እንደ ምሳሌ በቅርቡ በኦሮሚያ ክልል በሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች የተከሰተው ዓይነት ብሔርን መሰረት ያደረገ ብጥብጥ ከፍተኛ ትርጉም አለው፡፡ አንድ አንዶች እንደሚያስቡት በአዲስ አበባ እና በዙሪያዋ ያሉ ከተሞች የተቀናጀ ማሰትር ፕላን ዝግጅት ነው ብለው አይወስዱትም፡፡ የዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተከራካሪዎችና የሰጋት ደረጃ የሚተነትኑ ድርጅቶች የሚያወጧቸው ሪፖርቶች ትርጉማቸው ከፍ ያለ ነው፡፡ በሀገሪቱ ውሰጥ ያለው የዲሞክራሲያዊ ሰርዓት በተለይም በየምርጫ ወቀት የሚፈጠሩ ሰጋቶች፤ መንግሰት የሚያወጣቸው አዋጆች፣ ደንቦች እና መመሪያዎች ተገማችነት፤ በአጠቃላይ ለኢንቨስትመንት ያለው ምቹ ሁኔታ ወሳኝ ግብዓቶች ናቸው፡፡ ዝም ብሎ በኢቲቪ የሚለፈፍ የገፅታ ግንባታ ፕሮፓጋንዳ ተጠቅመው የኢንቨስትምነት ውሳኔ አይሰጡም፡፡

በተቃራኒው የቻይና መንግሰት በከፍተኛ ደረጃ አፍሪካን ለመቆጣጠር ባለው ፍላጎት መነሻ እንዲሁም ውሳኔ የሚሰጡት የግል ባለሀብቶች ሳይሆን የቻይና መንግሰት በመሆኑ ውሳኔዎች በአብዛኛው ኤኮኖሚያዊ አዋጭነት ብቻ ሳይሆኑ የፖለቲካ ጭምር ናቸው፡፡ በአሁኑ ጊዜ ቻይና በዓለም ላይ ከፍተኛ ብድር ሰጪ ሀገር ነች፡፡ ለአማሪካ ጭምር፡፡ በቻይና የግል ሴክተሮች በዓለም አቀፍ ደረጃ ኢንቨስት ለማድረግ ገና አልደረሱም፡፡ ቻይና እንደ ሀገር ያላትን ከፍተኛ ቁጠባ በዓለም ላይ ኢንቨስት ለማድረግ እየተጠቀመችበት ነው፡፡ ቻይና በሙሉ በሚባል ደረጃ የምትሰጠንን ብድር የሚጠቀሙበት የቻይና ኩባንያዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ኩባንያዎች ያለውን ስጋት በሚያካክስ ደረጃ ትርፋቸውን በአጭር ጊዜ ለማግኘት ይገባሉ በአሁኑ ሰዓት ቴሌን የወሰዱት ሁለት የቻይና የመንግስ ኩባንያዎች ናቸው፡፡ በተለያየ ስም የሚሰሩ፡፡ ቻይና የምታስገርመው እነዚህ የመንግሰት ኩባንያዎች ጉቦ የመሰጠት ጭምር አቅም አላቸው፡፡

እንደ ማጠቃለያ ለኢትዮጵያ የተበጀተው በጀት ብር 178.6 ቢሊዮን በጀት እንደ ሀገር ሲታይ አጅግ ዝቅተኛ ነው፡፡ ኢትዮጵያ 90 ሚሊዮን ህዝብ የሚኖርባት ከመሆኗ አንፃር እና በቅርቡ ደግሞ ዓመታዊ የነብስ ወከፍ ገቢያችን ብር 11 ሺ (550 የአሜሪካዶላር) ደርሶዋል ከተባልን ይህ በጀት ከእያንዳንዱ ሰው በወር የገቢውን 1.5 ከመቶ መዋጮ ሊሸፍነው የሚችለው ነው፡፡

ቸር ይግጠመን

No comments:

Post a Comment