Wednesday, March 5, 2014

ከፍተኛ የመንግስት ፕሮቶኮል ሹም ከስልጣን ተነሱ(ከኢየሩሳሌም አርአያ)


March 5, 2014
በኢ.ፌ.ዲ.ሪ መንግስት ከፍተኛ የፕሮቶኮል ዋና ሹም ሆነው ሲያገለግሉ የቆዩት አቶ በላይ ግርማይ ከስልጣን መነሳታቸውን የቅርብ ምንጮች ገለፁ። የሕወሐት አባል የሆኑትና ከ1990ዓ.ም ጀምሮ የጠ/ሚ/ሩ እንዲሁም የፕሬዝዳንቱ ፕሮቶኮል ሹም ሆነው በአቶ መለስ ዜናዊ ተሾመው ሲያገልግሉ መቆየታቸውን ያስታወቁት ምንጮች የአቶ በላይ ቢሮ በውጭ ጉዳይ ሚ/ር ውስጥ እንደነበረ ጠቁመዋል። የቀድሞ ፕ/ት ነጋሶ ጊዳዳ፣ የጠ/ሚ/ር መለስ ዜናዊ እንዲሁም የፕ/ት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ የፕሮቶኮል ሹም ሆነው ሲያገለግሉ መቆየታቸውን ያስታወሱት ምንጮቹ፣የውጭ አገር ባለስልጣናት፣ አምባሳደራትና ሌሎች አካላት ወደ ጠ/ሚ/ሩም ሆነ ፕሬዝዳንቱ ከመግባታቸው በፊት ጉዳያቸው በአቶ በላይ ግርማይ በኩል ያልፍ እንደነበር አያይዘው ገልፀዋል።
ጠ/ሚ/ር መለስ ዜናዊ ሕይወታቸው እስካለፈበት ጊዜ ድረስ ለ14 አመት በከፍተኛ ፕሮቶኮል ሹምነት ሲያገለግሉ የቆዩት አቶ በላይ ለአቶ መለስ ከነበራቸው ታማኝነትና ቀረቤታ አንፃር ከጠ/ሚ/ሩ ሞት በኋላ በነበራቸው ስልጣን ብዙም ደስተኛ እንዳልነበሩ የጠቆሙት ምንጮች አክለውም በሕወሐት ውስጥ ተፈጥሮ ከቆየው የቡድን ልዩነት ጋር በተያያዘ አቶ በላይ ግርማይ ከሃላፊነት እንዲነሱ በነደብረፂዮን መወሰኑን አስታውቀዋል።
በሌላም በኩል ለአቶ በላይ ግርማይ ቅርብ የሆኑ ምንጮች እንደሚሉት በገዛ ፈቃዳቸው እንደለቀቁ ይጠቁማሉ። የአቶ መለስና የወ/ሮ አዜብ ታማኝ ከሚባሉት የአገር ውስጥ ደህንነት ዋና ሃላፊ ወ/ስላሴ ወ/ሚካኤል ከስልጣን ተነስተው በሙስና እስር ቤት መወርወራቸውን፣ እንዲሁም የቤተመንግስት የደህንነትና ጥበቃ ዋና ሃላፊ አቶ ጌታቸው ተፈሪ ቀጥሎ ከስልጣን የተነሱ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣን አቶ በላይ ግርማይ እንደሆኑ ምንጮቹ ገልፀዋል። አቶ በላይ ግርማይ የጋዜጠኛ ብርቱካን ሃረገወይን ባለቤት ሲሆኑ፣ ጋዜጠኛ ብርቱካን በኢትዮጲያ ራዲዮና ቴሌቪዥን በሃላፊነት ተመድባ የምትሰራና አቶ መለስ ዜናዊን ብዙ ጊዜ ለብቻዋ ቃለምልልስ ታደርግ እንደነበረ፣ እንዲሁም ከጠ/ሚ/ሩ ጋር ወደ ተለያዩ አገራት አብራ ትጓዝ እንደነበረ ምንጮቹ አመልክተዋል።

No comments:

Post a Comment