Thursday, April 10, 2014

ብርሃኑ ዳምጤ – ደቡር፣ አባ መላ፣ ዘ-አገምጃ April 9, 2014

መስፍን ቀጮ/ወፍ

የሚቀጥለውን ትረካ ለመጻፍ ብዙ ሀሳብ ውስጥ ገብቼ ነበር፡፡ ብጽፈውስ ምን ዋጋ አለው የሚል ስሜትም ተጭኖኝ ነበር፡፡ ሆኖም ‹ጅብ በማያውቁት ሀገር ቁርበት አንጥፋልኝ› እንዲሉ ከላይ የተጠቀሰው ብርሃኑ ደቡር አባ መላ በአዲሶቹ አለቆቹ የተረቀቁለትን ቃለ መጠይቆች ሲያነበንብ መስማቱ ስለሰለቸኝ ‹ማን ያውጋ የነበረ ማን ያርዳ የቀበረ› በማለት የልጅነት ጓደኛዬን ሳልወድ ለማጋለጥ ወሰንኩ፡፡Berhanu Damte Ethiopian regime supporter
እኔና ብርሃኑ ዳምጤ በአንድ ማዕድ እየበላን በሰፈር ወንዝ እየተራጨን እየተንቦራጨቅን ብይና አርቦሽ እየተጫወትን ሌላም ሌላም ነገር እየሰራን ያደግን ልጆች ነበርን፡፡ ብርሃኑና እኔ ት/ቤት ስንገናኝ እንዲሁ ጓደኛሞች ሆነን እኔ ከእሱ በዕድሜ አራት ዓመት አንስ ስለነበር ትምህርት የጀመርኩት ከሱ በኋላ ነበር፡፡ አንደኛ ክፍል ስገባ እሱ ወደሶስተኛ ተዛውሯል፡፡ ከሱ በእድሜ ከማነሴ በላይ ደቃቃ በመሆኔ ‹ቀጮ› የሚል ቅፅል ስም ወጥቶልኝ ነበር፡፡ ብርሃኑ በዚያን ጊዜ ከክፍል ልጆች በዕድሜ ይበልጥ ነበር፡፡ በትምህርቱ ደካማ ስለነበር ክፍል ስለሚደግም ታናናሾቹ ይደርሱበትም ይቀድሙትም ነበር፡፡ ለዚህም ነው እኔና እሱ ስድስተኛ ክፍል ላይ የተገናኘነው ብርሃኑ በጣም ወፍራምና ለፍላፊ ነበር፡፡
ሲለፈልፍ በፍንጭቱ ይረጨው የነበረው ምራቅ ከውፍረቱ ጋር ሆኖ ትርክርክነቱን ያጎላው ነበር፡፡ አንድ የጠቅላይ ግዛት ልጅ ‹የድሃ መሃቻ› (ሊጥ ማቡኪያ) ብሎ ጠራው፡፡ ከዚያ በኋላ የድብቅ መጠሪያ ስሙ ሆነ፡፡ ብርሃኑ ምግብ በተለይ ጥሬ ሥጋና እንቅልፍ ከሁሉም በላይ አብልጦ የሚወድ ልጅ ነበር፡፡
ከስድስተኛ ክፍል በኋላ እኔና ብርሃኑ በጣም ጥብቅ ጓደኛሞች ሆንን ብርሃኑን የተጠጋሁት የሰፈር ጉልቤዎች በሚተናኮሉኝ ጊዜ ይከላከልልኝ ስለነበር እሱ የወደደኝ ደግሞ ክፍል ውስጥ የቤት ስራም ሆነ ፈተና ስለማስገለብጠው ከዚያም አልፎ ከትምህርት ቤት በኋላ እቤቴ ሸኝቶኝ ምግብ በልቶ ስለሚሄድ ነበር፡፡ በወላጆቼ በኩል ከቀልደኝነቱ ባሻገር አንድ ልጃቸው በመሆኔ እንደ አይነ ብሌናቸው ያዩኝ ስለነበር ወንድም በማግኘቴ ደስ ብሏቸው ይወዱት ነበር፡፡
የስድስተኛ ክፍል ሚኒስትሪ ተፈትነን ውጤት ሳንሰማ በክረምት ወር አባቴ በመስሪያ ቤቱ ትዕዛዝ ወደ ጠቅላይ ግዛት በመዛወሩ እኔም አብሬ ተጓዝኩ፡፡ በሶስተኛ ዓመት ክረምት ላይ ለዕረፍት አዲስ አበባ መጥቼ ስለነበር ጓደኛዬን ለማግኘት ሰፈር ስሄድ አያቶቹን ሊጠይቅ አገምጃ ጉራጌና ኦሮሞ አገር መሄዱ ተነገረኝ፡፡ በነገራችን ላይ ብርሃኑ በአባቱ መንዜ ሲሆን በእናቱ ደግሞ የአገምጃ ጉራጌና ኦሮሞ ነው፡፡ ሳላገኘው በመመለሴ እያዘንኩ ወደ ጠቅላይ ግዛት ተመለስኩ፡፡ በዓመቱ አባቴ እንደገና ወደ አዲስ አበባ በመዛወሩ ተመልሼ አዲስ አበባ መጣሁ ብርሃኑንም ወዲያው አገኘሁት፡፡
ብዙ ገጠመኞቻችንን እየተለዋወጥን እንደቀድሟችን አብረን መጫወትና መዋል ቀጠልን፡፡ ታዲያ መስከረም ጠባና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርታችንን ስንጀምር እኔ ከአስረኛ ክፍል ልጆች ጋር ስሰለፍ ጓደኛዬ ከዘጠነኞች ጋር ተሰልፎ አየሁት፡፡ ሚኒስትሪ በመውደቁ አንድ ዓመት ደግሟል፡፡ አልገረመኝም ጓደኛዬን ስለማውቀው!
ከስልሳዎቹ መጀመሪያ የኃይለስላሴ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች የሚያንቀሳቅሱት የመንግስት ተቃውሞና አመጽ እየበረታ  በሄደበት ወቅት የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎችን ቀልብ ስቦ የእንቅስቃሴው አጋርና ደጀን አድርጓቸው እንደነበር ይታወሳል፡፡ ስድስትና አራት ኪሎ በተነቃነቁ ቁጥር መላው የአዲስ አበባ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ይንቀሳቀሳሉ፡፡ ወረቀት ይበተናል፣ የከተማ አውቶቢስ ይሰባበራል፡፡ ሌላም ብዙ ሌላ ነገር ይደረጋል፡፡ በዚያን ወቅት የመርካቶን ተማሪዎች የምናስተባብረው ብርሃኑ፣ እኔ፣ ተስፋዬ የማነና ሌሎም ነበርን፡፡ ተስፋዬ የማነ ችኩል ቅብጥብጥ ግብታዊና ደፋር ነበር፡፡ ይህን ስለምናውቅ አደገኛ ሁኔታዎችን እንዲፈጽም እናደርገው ነበር፡፡ አንድ የማልረሳውና እስከ አሁን ድረስ የሚፀጽተኝ ነገር ላውራችሁ፡፡ ከሰፈር ወጥተን ልክ ጠቅላይ ቢሮ ስንደርስ ሹፌሩ ብቻ ያለበት አንድ አውቶቢስ ቆሞ እናያለን፡፡ አውቶቢሱ ብቻ ለምን እንሰብራለን ሹፌሩም መመታት አለበት አለ ብርሃኑ ችኩልና ቅብጥብጡ ተስፋዬ ዕብድ በሚያክል ድንጋይ የሾፌሩን አናት ተረከከው፡፡ ምስኪኑ ሹፌር
የተማሪዎች እንቅስቃሴ ተጠናክሮ የየካቲትን አመጽ አስከተለ፡፡ አመጹ በመካሄዱ ላይ እንዳለ ከውጪ የመጡ ምሁራንና የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች በየፊናቸው ሕቡዕ ጥናት ክበቦችን በማቋቋም ወጣቱን መመልመል ተያያዙት፡፡ በዚህም መሰረት ኢህአፓና መኢሶን ወጣቱን እየተቀራመቱ በየጎራቸው ኮለኮሉት ታዲያ ብርሃኑ፤ ተስፋዬና እኔ የኢህአፓ ሰለባዎች ሆንን፡፡ እንደማንኛውም ወጣት የድርጅቱ ተገዢና ደጀን ለመሆን በሙሉ ልብ ተሰናዳን፡፡ ከብዙ ፈተናና ምስጢራዊ ግምገማ በኋላ ታማኝነታችን በመረጋገጡ ከበላይ አካል የሚሰጠንን ሚሽኑ (ግዳጅ መፈጸም ጀመርን) በዚህ ወቅት ነበር፡፡ ብርሃኑ ዳምጤ ‹‹ደቡር›› የተሰኘውን የኮድ ስም የተጎናጸፈው እኔም ከቀጮ ወደ ‹‹ወፍ›› ተቀየርኩ፡፡ የተስፋዬን ረሳሁት፡፡ በድርጅቱ መዋቅር መሠረት እኔ በቅርብ እንዳውቃቸው የተደረጉት ተስፋዬና ብርሃኑ ደቡር ብቻ ነበሩ፡፡ በደቡር በኩል እየተነገረኝ ከበላይ የሚፈሰውን መመሪያና ግዳጅ መፈጸም የቀን ተቀን ተግባራችን ሆነ፡፡
ከትዝታዎቹ አንድ ቀን ደቡር ግዳጃችንን ነገረን ይኸውም ምዕራብ ሆቴል ጀርባ አንድ ሀብታም ነጋዴ የቀን ገቢውን ማታ ማታ ቤቱ ይዞ ስለሚሄድ መኪናው አካባቢ በመቆየት ገንዘቡን ተረክቦ መሄድ ስለሚሆን ሁለት የታጠቁ ጓዶች በአካባቢው እንደሚገኙና ወፍ የተቀዳደደ ልብስ ለብሰህ ማዘናጋት ትጀምራለህ ተባልኩ፡፡ ወዲያውም ጓዶቹ አስፈላጊውን እርምጃ ይወስዳሉ፡፡ ሰውየውን ገና ስጠጋው ጓዶቹ ከመቅጽበት መጥተው ገንዘብ ተረክበው ይባስ ብለው የሰውየውን ፔጆ መኪና ቁልፍ ነጥቀው አስነስተው ፈረጠጡ ወደ መደበቂያችን ቦታ ሄድኩ፡፡ ደቡርና ተስፋዬ ቤቱን አሟሙቀው ጫት እየቃሙ ደረስኩ፡፡ በምርቃና የተለያዩ እቅዶችን ስናወጣና ስናወርድ ቆይተን ወደ ጨብሲ ተዘዋወርን፡፡ ብዙ ስንገነባና ስናፈርስ አድረን፡፡ የበላይ አካልን ትዕዛዝ እንጠብቃለን፡፡ ራሳችን በግብታዊነት፣ በጠላት ስም ሰዎችን እረሽነናል፡፡ ሚሽን ከሌለን ሥጋ መጠጥና ጫት አስገዝተን ለሌላ ግድያ እንዘጋጃለን፡፡ ቀልቤሳ በቀበሌ የኛ ግፍና ጭካኔ ደግሞ ከሱ ቢበልጥ እንጂ አያንስም፤ ምን ዋጋ አለው ለአንባቢያን ማቅረቡ እኔን ራሴን ስለሚዘገንነኝ ዝም ብዮ እዘጋዋለሁ፡፡ ባለፈረሱ ብርሃኑ ደቡርስ ምን ይሰማው ይሆን? እንደ አርበኞችና ጀግኖች እሱም ባለፈረስ ሆነ አባነብሱ፣ አባዳኜ፣ አባጠቅል፣ ሲባል ሰምቶ ብኩን አረመኔ!
ትግሉ እየጋለ በሄደ ቁጥር የመኢሶንና የኢህአፓ ጦርነት እየተፋፋመ ሄደ፡፡ በዚህም ጊዜ ራስን ለማዳን ወይም ለአላማ ብዙ ጓዶች ተገድለዋል፡፡ እኛም ብዙ ረፍርፈናል፡፡ ብዙ ሀብታሞችን አስገብረናል፡፡ የንጹህ ሰዎችንም ደም በከንቱ አፍሰናል፡፡ ቤት ይቁጠረው፡፡ ከአሜሪካን ግቢ ጀምሮ አደሬ ሰፈርን ሰባተኛን ኮልፌን አካሎ በአሸባሪነትና በገዳይነት የታወቀው ስም ደቡር የዛሬው አባመላ ከነህዋሱ ነበር፡፡ ሁኔታዎች እየከፉ ሄደው በቀበሌና በደርግ ፖሊሶች ኢህአፓ፣ መመታት ጀመረ፡፡ ይባስ ብሎም ኢህአፓ ለሁለት ተከፈለ፡፡ በመሆኑም የኢህአፓ መዋቅር ውዝምብር ውስጥ በመግባቱ ግማሹ ወደ አሲንባ፣ ሸዋና ወሎ ገጠር ውስጥ ሲገባ ግማሹ ደግሞ ከተሞች ውስጥ መፍጨርጨር ጀመረ፡፡ እኔ አዲስ አበባ ስቀር ደቡርና ተስፋዬ ወደ አጋምጃ ሸፈቱ፡፡ ሩቅ ሳይሄዱ አንዲት ትንሽ ሆቴል አልቤርጎ ውስጥ ተማርከው ወደ አዲስ አበባ ተወሰዱ፡፡ ወሬውን ስሰማ በጣም አዘንኩ፣ ተደናገጥኩ፡፡ ተደብቆ መኖርንም ተያያዝኩት፡፡ ከጥቂት ወራቶች በኋላ ተስፋዬን አገኘሁት፡፡ እንደኔው ተጨናንቆና ተደናግጦ ነበር፡፡ ከእስር እንዴት እንደተፈታ አላጫወተኝም፡፡ የመጨረሻ መተያየት ሆነ፡፡ ሰንብቼ ስጠይቅ ተስፋዬ የማነን እህቶቹ ወደ አሜሪካ እንደወሰዱት ሰማሁ፡፡ አይ ቅብጥብጡ ተስፋዬ አሁንስ ሰክኖ ይሆን?
ከኢህአፓ መሰነጣጠቅ በኋላ ብዙ ጓዶች ለደርግ እጃቸውን ሰጡ ይቅርታ እየጠየቁ፡፡ አንድ ምሽት በተደበቁበት ቦታ ከብርሃኑ ደቡር የኮድ መልዕክት ደረሰኝ፡፡ በጣም በመገረም ወደ ቀጠሮው ቦታ ሄድኩ፡፡ በኮድ መሠረት ወደተባለችው ላንድክሩዘር ተጠጋሁ፡፡ ደቡር ጋር አይን ለአይን ተያየን፡፡ መኪናው ውስጥ ገባህ ተሳሳምን፡፡ መኪናዋ መንቀሳቀስ ጀመረች፡፡ ከጥቂት ቆይታ በኋላ መኪናውን ከሚሾፍረው ሰው ጋር አስተዋወቀኝ፡፡ ቀጥሎም መጠነኛ የፖለቲካ ትንታኔ ካደረገልኝ በኋላ ግራ የሚያጋባ ሚሽን (ግዳጅ) እንዳለን ገለጸልኝ፡፡ ይኸውም ጓዳችን የሆነው ጩልሌ (መላኩ) መመታት እንዳለበት በበላይ አካል መወሰኑን ነገረኝ፡፡ ጥርጣሬ ላይ ወደቅሁ፡፡ በማን? በደርግ? ወይስ ከሁለቱ የኢህአፓ አንጃዎች ባንዱ? ግራ ገባኝ፡፡ ብርሃኑ ደቡርና ሰውየው ጉንጫቸው በጫት ተወጥሮ ነበር፡፡ ጨብሲ እናድርግ ብለው ሰንጋ ተራ አካባቢ መኪናዋን አቆሙ፤ አንዲት ትንሽ መጠጥ ቤት ገብተን ቢራዎች መጠጣት ጀመርን፡፡ ከሁለት ሰዓት ቆይታ በኋላ ከቤቷ ወጥተን ወደ ተክለሃይማኖት አቀናን ጎላ ሰፈርን እንዳለፍን የተዋወቅኩት ሾፌር መኪናዋን አቁሞ ወረደ፤ ከመንገዱ ዳር ካለች የተዘጋች ኪዩስክ ጠጋ ብሎ ከአንድ ህፃን ጋር ተነጋግሮ ወደ መኪናው ተመለሰ፡፡ ወዲያውኑ ደቡር ክላሽንኮቭን ከመኪናው ወለል አንስቶ የመኪናውን የጎን መስታዋት አወረደ፡፡ ከትንሽ ደቂቃዎች በኋላ ጩልሌ (መላኩ) ከመንገዱ ዳር ሲደርስ ብርሃኑ ደቡር የያዘውን ክላሽ አቅንቶ ጥይቱን አርከፈከፈበት፡፡ በሰኮንዶች ጊዜ ብትንትኑ ወጥቶ መሬት ላይ ተዘረረ፡፡ መኪናዋም በሀይለኛ ፍጥነት እየበረረች ሰፈሩን ለቀቅን፡፡ ብዙ ግድያዎች ላይ ተሳትፌአለሁ፡፡ እንደዛች ቀን ግን ደንግጨና ፈርቼ አላውቅም፡፡ እስከዛሬ ህሊናዬን የሚያስጨንቀኝ ነገር ቢኖር ጩልሌን ለምን? ነበር፡፡
ደቡርስ አሁን ምን መልስ ይሰጠን ይሆን ወይስ እንደጲላጦስ እጁን ታጥቧል፡፡ ጉዞዋችንን በመቀጠል ፒያሳን ካቋረጥን በኋላ በራስ መኮንን ድልድይ አካባቢ እንደገና አንድ ቡና ቤት ውስጥ ገባን፡፡ እኔ እየተርበተበትኩ ነው፡፡ እነሱ ግን በጫቱና በጨብሲው ምክንያት የደፈረሱትንና ቦታ የጠበባቸውን አይኖቻቸውን እያጉረጠረጡ እንደገና አልኮል መገልበጥ ጀመሩ፡፡\ከትንሽ ጊዜ በኋላ ብርሃኑ ወሬውን ቅደድ ጀመረ፡፡ የኢህአፓን ከንቱነትና መፈረካከስ አመራሩን እየኮነነ ከዘላበደ በኋላ በሱ እምነት ደርግ ጋር ተጠግቶ በኢህአፓ ላይ ቀይ ሽብር ማፋፋም የወቅቱ አንገብጋቢ ጥያቄ መሆኑን ገለጸልኝ፡፡ አያይዞም የጩልሌ እምቢታ ምን እንዳመጣበት አበክሮ አሳሰበኝ፡፡ ላብ በላብ ሆኜ እየተብረከረኩ እምቢታዬን ገለጽኩለት፡፡ ብዙ ሊያግባባኝ ሞከረ፡፡ ምንም እንኳ በሁኔታው ብደናገጥና ብፈራም ፍንክች አላልኩለትም ነበር፡፡ በግልጽም ነገረኝ፡፡ በጨካኙ የደርግ ምርመራ ሹም በሻለቃ ብርሃኑ ከበደ ሥር እንደሚሰራና ብዙ የኢህአፓ ጓዶችን ወደ ደርግና ወደአብዮቱ እንዲመለስና እምቢተኞችም እንዳስመታ ገለጸልኝ፡፡ አሁን ተደናገጥኩ ፍርሃቴም ቀጠለ፡፡ ብርክ ያዘኝ ከህሊናየ ጋር እየተሟከትኩ ቡና ቤቱን ለቀቅን፡፡ መኪናዋ ወደ አራት ኪሎ አመራች፡፡ በመካከላችን ፀጥታ ሸፍኗል በመጨረሻም ሰተት ብላ ሚኒልክ ግቢ ገባች፡፡ ከመኪና ወረድን በእግራችን ትንሽ ከሄድን በኋላ አንድ በጩኸትና በለቅሶ የተሞላ ቤት በረንዳ ላይ አስቀመጡኝ፡፡ ከጥቂት ቆይታ በኋላ አንድ የሰከረ መርማሪ በጥፊ እያዳፉ አንዲት ጠባብ ክፍል ውስጥ አስገብቶ አግዳሚ እንጨት ላይ ገልብጦኝ፡፡ ወዲያውኑ አንዲት በደም የተጨማለቀች ኳስ ቢጤ አንስቶ ወደ አፌ ሊወትፍ ሲል ብርሃኑ ደቡር ብቅ አለና ስሙን ጠርቶ ቆይ አለው፡፡ በቅጽበታዊ ገለል ብሎ ቆመ፡፡ ከሁኔታው ደቡር አለቃው መሆኑን ተረዳሁ፡፡ ‹‹እሱን ለኔ ተወው›› በማለት ከመጀመሪያው ጥፊ በቀር ተገልብጦ አዳነኝ፡፡ ብርሃኑ ደቡር ጓደኛዬን ማመን አቃተኝ የአብሮ አደግነት ቆሌ ከሰባተኛ ተነስታ መርካቶን ፒያሳን  ቤተመንግስት ገብታ አዳነችኝ፡፡ ክብር ምስጋና ይግባትና ከዚያ በኋላ አንድ በእስረኞች የተጣበበች ግማት በግማት ክፍል ውስጥ አጎሮኝ ተሰወረ፡፡ እዚያች ጠባብ ግም ክፍል ውጥ የሚዘገንኑ ትርኢቶች አጋጠመኝ አንድ ሁለቱ አዲስ ግርፎች ስለነበሩ ነባር እስረኞች ቁስላቸውን በቆሻሻ  ጨርቅ ሲጠርጉና ሲሸፍኑላቸው ተመለከትኩ፡፡ ቁስለኞቹም የስቃይ ድምጽና ለቅሶ ሲያሰሙ ታዘብኩ፡፡ በአጠቃላይ ሀያ ከሚሆኑ እስረኞች መሀል ሳልገረፍ የገባሁት እኔ ብቻ ነበርኩ፡፡ አይ! የመርካቶዋ አድባር ቆሌ! ሺህ አድባር ውለታሽን ይክፈሉሽ አልኩ በልቤ፡፡ እዚያች ክፍል ውስጥ ሳለሁ ከተመለከትኩት አዲስ ቁስለኛ ሲመጣ የከረመው ወደ ሌላ ቦታ ይወሰዳል፡፡ ማገገሚያ ጣቢያ አይነት ነበረችና አንዳንዴም ባሳቻ ሰዓት የተወሰኑ ሰዎች ይወስዳሉ፡፡ ዕጣ ፋንታየ ምን እንደሆነ ሳላውቅ ይኸው አስር ቀን ሆነኝ፡፡ በአስራ አንደኛው ቀን ሰባት የምንሆን እስረኞች ስማችን እየተጠራ እንድንወጣ ተደረገ፡፡ ምን ይሆን እያልኩ ስጨነቅ ከሌላ ቦታ ከመጡ አምሳ ከሚሆኑ እስረኞች ጋር በአንድ አዳራሽ ውስጥ ተደባለቅን ከጥቂት ጊዜ በኋላ የስብሰባው አስተናባሪ የዕለቱን አንቂና ተናጋሪ በአንዲት በር በኩል አስከትሎት ገባ፡፡ ሌሎች ይወቁት አይወቁት እንጃ እኔ ግን ጓደኛየን ደቡርን ሳየው ስላላስገረፈኝ ከልቤ እያመስገንኩ የሚለውን ለመስማት በጉጉት መጠበቅ ጀመርኩ፡፡ ከንግግሩ ምንም የተለየ ነገር አልሰማሁም ያው እንደለመደው ኢህአፓን አጥብቆ አወገዘ ወደ አብዮቱ ካምፕ መመለስን አበክሮ ከአስገነዘበ በኋላ ምርምራችን ተጣርቶ ንጹህነታችን ስለተረጋገጠ ምህረት እንደተደረገልንና ከአሁን በኋላ ሰላማዊ ኑሮ እንድንጀምር አበክሮ ከአሳሰበን በኋላ ወዲያውኑ በተነን፡፡ ከደስታ ብዛት ግማሹ ያለቅሳል ሌላው ይስቃል አንዳንዱ ደግሞ የድጋፍ መፈክር ያሰማል ሳይጠየቅ ታዲያ ሌላ ምን ያድርግ? አይ የነፍስ ነገር የሆነው ሆኖ ከአዳራሹ ስንወጣ ደቡር ወደ ቢሮው ወሰደኝና ጥቂት ምክር ከሰጠኝ በኋላ ለታክሲና ለምግብ የሚሆን አስር ብር ሰጥቶኝ እንድሰወር ነገረኝ፡፡ አይ አብሮ ማደግ እያልኩ አመስግኘው ተለያየን፡፡
ህቡዕ በነበርኩበት ጊዜ ሁሉን ነገር በሬዲዮና በጋዜጣ እከታተል ነበር፡፡ በተለይም በ1968 እና በ1969 ኢህአፓ በከተማ ውስጥ በመደምሰሱ መኢሶንም ፍርጠጣውን ተያይዞት ስለነበር፤ ደርግ በነበረበት ፍልሚያ የውስጥ ተቀናቃኞችን መደምሰስና ማስወገድ ነበር፡፡ ባልታሰበ ሁኔታ ሰናይ ልኬና ኮሌኔል ዳንኤል አስፋው በሻለቃ ዩሃንስ እንደተገደሉ የወዝ ሊግ መዋቅር ከመቅጽበት ፍርስርሱ ወጣ፡፡ በወቅቱ በተራ ካድሬዎች ቀርቶ በራሳቸው በደርግ አባላት የሚፈራው ሻለቃ ብርሃኑ ከበደ የብርሃኑ ደቡርና የሌሎቹ መርማሪ ነፍስ ገዳዮች አለቃ ከወዝ አደር ሊግ መፈራረስ በኋላ ባንዲራው በመውደቁ ያ ጨካኝ አውሬ ነፍስ በላ በደርግ የመረሸን ፅዋ ደረሰው፡፡
በሁኔታው የተደናገጡት የወዝ ሊግ አመራር አባላት ይቅርታ እየጠየቁ ለመንግስቱ ሀይለማርያም ገበሩ በተዋረዱም ብርሃኑ ደቡርና መሰል ጓደኞቹ አለቃቸውን ሻለቃ ብርሃኑ ከበደን እየኮነኑና እያወገዙ ነጻ ሆኑ የዛን ጊዜዎቹ ጲላጦሶች! ደቡር ለተወሰነ ጊዜ ድምፁ ጠፋ፡፡ እንደ እኔ ህቡዕ ገባ ወይስ ከአገር ወጣ እያልኩ አብሰለስል ነበር፡፡
ከወራቶች በኋላ የዳምጤ ልጅ ደቡር የሰደን ካባ ለብሶ ከፍተኛ ካድሬነት መከሰቱ ሰማሁ፡፡ ‹‹ለሆዳም በሬ ጭድ ያዝለታል›› እንዲሉ ብዙ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ በሚካሄድበት ፒያሳ አካባቢ ነበር የተመደበው፡፡ እሳቱ ደቡር በስልጣኑ በመመካትና በማስፈራራት ብዙ ገንዘብ ዘርፏል፡፡ በነፃ ከሚጠጣውና ከሚመገበው ባሻገር በጣም የሚያሳዝነው እሱና ግብረ አበሮቹ በፀረ አብዮት ሰበብ ብዙ ወጣት ልጃገረዶችን እያሰሩ ደፍረዋል፣ አበላሽተዋል፡፡ በርብርቦሽ አባት አልባ ልጆችን አስወልደዋል፡፡ የርብርቦሽ ዲቃላዎች ማሳደግ አቅቷቸዋል፡፡ ብርሃኑ ደቡር በየሆቴሉ እየገባ በነፃ መብላትና መጠጣት መብቱ አድርጎት ነበር፡፡ ካስቴሊ በነፃ ይመግበውና ያጠጣው ነበር፡፡ ከምግብ ሁሉ ጥሬ ሥጋ አብልጦ ስለሚወድ በአራዳ ልኳንዳ ቤቶች በነፃ ትኩስ ብልቶች መብላት ሥራው ነበር፡፡ ሆዳም! ይህም ድርጊቱ የአደባባይ ምስጢር እየሆነ በመምጣቱ በቀንደኛው ደርግ አባልና የሰደድ የበላይ አካል በጋሻው አታላይ ክትትል እንዲደረግበት ታዘዘ፡፡ ክትትሉ ውጤት አስገኘ ኮንትኔንታል ቡና ቤት አጠገብ ወደ እርይ በከንቱ መውረጃ ላይ ፒዜሪያ የምትባል የጣሊያን ምግብ ቤት አለች፡፡ ጣልያናዊው ባለቤት ከለውጡ በኋላ ለላብ አደሮቹ መርቆ አገር ለቆ ሄደ፡፡ ላብአደሮቹ ለጥቂት ጊዜ አብረው ከሠሩ በኋላ በስምምነት ኤርትራዊ ላብአደር ምግብ ቤቱን ጠቅልለው ይህ ሰው በአካባቢው ቀበሌ ተመራጮች በፈለጉት ጊዜ መጥተው በነፃ ይመገቡ ጀመር፡፡ በተጨማሪም ገንዘብ ያስገብሩት ነበር፡፡ ችግሩን መሸከም ሲያቅተው በሰዎች ምክር አቤቱታውን ለከፍተኛው ካድሬ አሰማ፡፡ ደቡር አጋጣሚውን በጣም ወደደው፡፡ ቀበሌዎችን አስፈራርቶ ዘረፋውን አስቆመ፡፡ በምትኩ ቀበሌዎቹን ተክቶ በተራው ምግብ መጠጥና ገንዘብ መብላትና መጠጣት መዝረፍ ጀመረ፡፡
ይህ ሲሆን የቀበሌ ተመራጮቹ አልተኙለትም ነበር፡፡ ብዙ ጭብጥ መረጃዎች አጠናቅረው ለበጋሻው አታላዩ አቀረቡለት፡፡ የዳምጤ ልጅ እንደለመደው ፒዜሪያ ገብቶ ሰዎች ጋብዞ እየበላና እየጠጣ ተዝናንቶ ሲወጣ እጅ ወደላይ ተብሎ በቁጥጥር ስር ዋለ፡፡ በማግስቱ በኢትዮጵያ ሬዲዮ ሆዳሙ ካድሬ ብርሃኑ ዳምጤ በሚል መግለጫ ግፉና ድርጊቱ ተነበበ፡፡ ከጥቂት ወራቶች እስር በኋላ በምህረት ተፈታ እስሩን አላከረሩበትም፡፡ ሁሉም ካድሬዎች የሱ አይነት ድርጊት  ይፈጽሙ ስለነበር፡፡ ከተፈታ በኋላ በአንዳንድ ጓደኞቹ እርዳታ ግብርና ሚኒስቴር ተቀጥሮ አጋርፋ እርሻ ማዕከል ተመደበ፡፡ እዚያ እየሰራ ሳለ እንደገና ታሰረ ምክንያቱን አላውቅም፡፡ በብዙ አማላጅና በሚኒስትሩ በዶክተር ገረመው ደበሌ ግፊት በእስር ተፈትቶ ወደ አዲስ አበባ ተመለሰ፡፡ በወቅቱ ደርግ በመላው ምስራቅ አውሮፓ ኮሚኒስት አገሮች የፖለቲካ ስልጠና እንዲገኙ ካድሬዎችን ይልክ ነበር፡፡ ታዲያ ቀልጣፋው ብርሃኑ ደቡር ተሰባብሮ ከአንድ ቡድን ጋር ወደሶቭየት ዩኒየን ለአስር ወራቶች የፖለቲካ ትምህር ተላከ፡፡ ከትምህርት መልስ ግብርና ሚኒስትር ተመለሰ፡፡ ሥራውን ጀመረ፡፡ ትንሽ ሰንበት ብሎ ወደ ዋናው ግብርና ሚኒስቴር ዕቃ ግዢ ክፍል ተመድበ፡፡ በመሆኑም ለሆዳሙ ጓደኛዬ ደቡር ሌላ አመቺ የዝርፊያ ሁኔታ ፈጠረለት፡፡ ከነጋዴዎች ጋር በመስማማት ገንዘብ ማካበት ጀመረ፡፡ ምርጥ ምርጥ ልብሶችና ጫማዎች መቀያየር ጀመረ፡፡ ቀን በቀን በውስኪ መታጠብ ጀመረ፡፡ በ247 ብር ደሞዝ ደርግ ድንብርብር ባለበት ዘመን ብዙ ፕሮግራሞ ያወጣ ነበር፡፡ በዚህም መሠረት የኢሠፓን ካድሬዎች ለልማትና ለመንደር ምስረታ በሚል በየክፍለሀገሩ በተበተነበት ጊዜ ብርሃኑ ወደ ጎጃም ክፍለ ሀገር ዘመተ፡፡ ተልዕኮውን ጨርሶ ሲመለስ አጅሬ ደቡር ‹‹ምን ይገደው›› ተገለባብጦ የኢሰፓ የአባልነት ቀይ ደብተር እጁ ውስጥ አስገባ፡፡ በዚህም ቀይ ደብተር ብዙ ነገደበት፡፡ ዘረፈበት ሌላም ሌላም ብዙ አደረገበት፡፡ ትዝ ከሚሉኝ አንዱ የግርማ ቢራቱ ነገር ነበር፡፡ ግርማ ቢራቱ የአባቱን ንግድ መርካቶ ውስጥ ያካሂዱ ነበር፡፡ ደስተኛ፣ ተጫዋች ሴት አሳዳጁና መጠጥ ወዳጁ ግርማ በጊዜው ተገጥሞለት ነበር
‹‹ከሰው ግርማ ቢራቱ
ከመኪና ቶዮታ ማርክ ቱ››
የዘመኑ የመርካቶና የአራዳ ልጆች ያስታውሱታል ብዮ አምናለሁ፡፡ ሞቷል ነፍሱን ይማረውና ታዲያ የብርሃኑ የገንዘብ ምንጭ ሆኖ ነበር፡፡ ወዶ ሳይሆን በመፍራት ሌሎች የሰፈራችን ነጋዴዎችና የቡና ቤት ሴት ባለቤቶች ገንዘብና ሩካቤ ስጋ ይለግሱት ነበር፡፡ ሳይወዱ በፍርሃት የደቡር ጉዞ ሁሌ እንደቀጠለ ነው፡፡ በተለመደው ‹‹አፍዝ አደንግዝ›› በነያሬድና በነአሳየ ብርሃኑ አማካይነት ደስ አለኝ ቤዛን ገልብጦ የግብርና ሚኒስቴር ቋሚ ካድሬ ሆነ፡፡ ደሞዙን ከ247 ብር ወደ 710 ተወረወረ ‹‹የባለ ማስትሬት›› ደሞዝ!!! ዶ/ር ገረመውን እያጫወተና እያሳቀ እንዳያፈናቅለው አደረገ፡፡ ይህም ሽፋን በዶክተሩ ስም እየነገደ ጉቦ መቀበል እንዲችል ረዳው፡፡ የግብርና ሚኒስቴርን የፋይናንስ መምሪያ ሃላፊዎች ብዙ ያልተወራረደ ገንዘብ እንዳለበት ተረጋግጦ እያለ እንዲመልስ አልተጠየቀም ካላበደ በቀር ማን ደፍሮ ሊጠይቅ! የብርሃኑ ዝርፊያ ብዙ አይነት ነበር፡፡ በብዙ መቶዎች የሚያስተናግደውን የሰራተኞች ክበብ መሪዎቹን አባሮ ክበቡን በቁጥጥሩ ሥራ ካደረገ በኋላ ከመርካቶ (ከሰፈሩ ሰባተኛ) ጩልሌ ልጆች ቀጥሮ የክበቡን ገቢ እየሰነጠቀ ሙልጭ አርጎ በልቷል፡፡ ሲሾም ያልበላ አይነት! ለምንስ አይዘርፍ ማን ሊጠይቀው! እንደገና ደርግ ሊወድቅ በሚንገዳገድበት ጊዜ የሞት የሽረቱን የኢትዮጵያን ወጣቶች እያስገደደ ለብሄራዊ ውትድርና ይመለምል ነበር፡፡ ካድሬዎች በየቀጠናው ኢሰፓ አንደኛ ፀሐፊዎች አመራር በኮሚቴ ምልመላውን ተያይዘውት ነበር፡፡ ብርሃኑ ደርቡም የአንዱ ቀጠና ኮሚቴ አባል ነበር፡፡ በወቅቱም ሀብታሞች ልጆቻቸው እንዳይዘምቱባቸው ለአንድ ልጅ እስከ 2000 ብር ይከፍሉ ነበር፡፡ እያንዳንዳቸው ቀጠናም የተወሰነ ኮታ መምታት ስለነበረበት ጉቦውን ከበሉ በኋላ በምትካቸው የድሃ ልጆችንና የጎዳና ተዳዳሪዎችን እያፈሱ ኮታቸውን ያሟሉ ነበር፡፡ ደቡርና መሰል ጓደኞቹ!
ብርሃኑ ደቦር የዳምጤ ልጅ ይሁን አባ መላ ምን ያላደረገው ነገር አለ፡፡ በስልጣኑ በመጠቀም መሬት ተመርቶ ጉለሌ ጳውሎስ ሆስፒታል ጀርባ ቪላ ቤት መሥራት ጀመረ፡፡ ቤቱም በሚያስደንቅ ሁኔታ በአጭር ጊዜ ውስጥ ተገባደደ፡፡ አያስገርምም፡፡ ጥሬ እቃዎቹ በሙሉ የተበረከቱት በልዩ ልዩ ነጋዴዎች ሲሆን መሃንዲዎቹና እንጨት ማገሩን የግብርና ሚኒስቴር ነበሩ፡፡ በነገራችን ላይ አምፑል እንኳን ከኪሱ አውጥቶ አልገዛም፡፡ ምላጩ ደቡር አባመላ በዚህ አላበቃም ቤት መሸጥ መለወጥ በተከለከለበት ዘመን አንድ ቀን እንኳ ያላደረበት ቤት ጠግሮ ዶላሩን አጥቁሮ ማንም ሳይሰማ ሽል ብሎ አሜሪካ ገባ፡፡
ያ ተበድሮ ያላወራረደው ገንዘብ በግብርና ሚኒስቴር የፋይናንስ ሰራተኞች ደመወዝ እየተቆረጠ ለመስሪያ ቤት ገቢ ተደረገ ‹‹አይጥ በበላ ዳዋ ተመታ›› አይነት!
ከላይ የብርሃኑ የዘር አመጣጥ የጠቀስኩት ያለ ምክንያት አልነበረም፡፡ ብርሃኑ የቀንደኛው ወያኔ ግልገል የግርማ ብሩ የአክስት ልጅ ነው፡፡ በሌላ ወገን ደግሞ ፕሬዚዳንት ግርማ ወልደጊዮርጊስ ለግርማ ብሩ አጎቱ ነው፡፡ በግርማ ወልደጊዮርጊስ ልጀምር ይቅርታ በአክብሮት ባለመጥራቴ አክብሮት አይገባውምና! ይህ ሰው ሁለት ዘመን እያምታታና እያጭበረበረ የኖረ ሲሆን አሁን በሶስተኛው መንግስት ፕሬዚዳንት ሆነ፡፡ በንጉሱ ዘመን የፓርላማ አባልነቱን ወደ ኋላ ትቼ በደርግ ጊዜ የፈፀማቸውን ድርጊቶች ላውሳ፡፡ የኤርትራ ክፍለ ሀገር ሲቪልአቪየሽን ሀላፊ ሆኖ ተሾመ፡፡ ከጥቂት አገልግሎት በኋላ በይዘቱም ይሁን በቅርፁ ከርሳሙ መቶ አለቃ ግርማ ተስባብሮ የኤርትራ የትራንስፖርት አላፊ ለመሆን በቃ ቦታውን የፈለገው ያለ ምክንያት አልነበረም፡፡ ‹‹ቦታው የወርቅ ማዕድን ነበርና›› በወቅቱ በደርግ አሰቃቂ ግፍ ምክንያት በሺዎች የሚቆጠሩ ኤርትራውያን ንብረታቸውን እየተው ሀገራቸውን ጥለው ወደ ውጪ ሀገር ወይም ወደበረሃ የሚጠፋበት ጊዜ ነበር፡፡ ምስኪኖች ሞትን ፈርተው! ‹‹ቀልጣፋው›› መቶ አለቃ ግርማ የየብሱና የባህሩ ትራንስፖርት ሀላፊው በመሆኑ የኤርትራውያኑን ምርጥ ምርጥ መኪናዎች ከምጽዋ አሰብ እየላከ በልጁ በሰለሞን ግርማ አማካኝነት አዲስ አበባ መሃል አገር እየቸበቸበ ብዙ ገንዘብ ካዝናው ውስጥ አስገብቷል፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፡፡ በልጁ ስም አንድ የንግድ ድርጅት አቋቁሞ ከሩቅ ምስራቅ የተዋጊ አውሮፕላኖችን መለዋወጫ የአውሮፕላን ቦንቦችና ሌላም ነገሮች መንግስት በማቅረብ ከፍተኛ ገንዘብ በኮሚሽን አግኝቷል፡፡ ‹‹ወያኔ እንደገባ በመገናኛ አውታሮች ሰለሞን ግርማ በወንጀል እንደሚፈለግ የለፈፈውን ያጤኗል እንደ አባት እንደልጅ እንዲሉ›› ሰለሞን ተቀለጣጥፎ ሩቅ ምስራቅ ኮበለለ፡፡ አሁን የት እንዳለ አላውቅም፡፡ መቶ አለቃ ግርማ ይበልጥ የሚታወቀው በስነ ምግባር ብልሹነቱና በሴሰኝነቱ ሲሆን የአስራ አራትና የአስራ አምስት እድሜ ያላቸውን ወጣቶች በሌሊት ሶስትና አራቱን እያበላሸ ያድር እንደነበር ይታወቃል፡፡
ለምሳሌ ያህል ከሁለት ወጣት እህትማማቾች ልጆች ማስወለዱም ይታወቃል፡፡ አብረኸት የተሰኘችውን የ12ኛ ክፍል ውሽማውን የምጽዋ ትራንስፖርት ሃላፊ በማድረግ የምሁራን ሠራተኞችን ሞራል አዳሽቋል ከርሳሙ መቶ አለቃ ግርማ የአሁኑ ፕሬዚዳንት! ያች ልጅ ‹‹Suger Dady›› ብላ የፃፈቸውን ያጤኗል፡፡
ግርማ ብሩን በተመለከተ ጎበዝ የቀለም ተማሪና በጣም ቀዝቃዛ ሰው ነበር፡፡ ከአብዮቱ ፍንዳታ በኋላ በኢህአፓነት ተጠርጥሮ ደብረዘይት ከተማ ታስሮ ሲያበቃ የተፈታ ነው፡፡ ዩኒቨርሲቲውን ከጨረሰ በኋላ አንገቱን ደፍቶ በሚኒስቴር መስሪያ ቤት ተቀጥሮ ወንበር ያሞቅ ነበር፡፡ ወያኔ ከገባ በኋላ ከአጎቱ ከግርማ (መቶ አለቃ) ጋር በመሆን የሶዶ ጅዳ ተወካይ በመሆን ተሽሎክልኮ ባልዋለበት የኦህዴድ አባል በመሆን እስከ ሚኒስቴርነት ደረሰ፡፡ ይህ የድንጋይ ስር እባብ ምን ያህል ጨቋኝ አድርባይ ስለመሆኑ የአደባባይ ሚስጥር ነውና ብዙ አልዘበዝብም፡፡ ለመሆኑ እነዚህ ሶስት ዘመዳም ጉዶች አጋምጃን ይወክላሉ? የባልቻ አባ ነፍሶ አገር እነዚህን ጎዶች ታብቅል? ባልቻ አባ ነፍሶስ ምን ይሰማው ይሆን መልሱን ለአባ  ነፍሶ አፅም ትቸዋለሁ፡፡
በቸር ይግጠመን
መስፍን ቀጮ/ወፍ
ከጠቅላይ ቢሮ
አዲስ አበባ

No comments:

Post a Comment