Sunday, January 18, 2015

የምርጫ ቦርድን ልጓም ማን ይግታው???

በእኔ እምነት ምርጫ ቦርድ ልጓሙን በጥሶ መፈርጠጥ ጀምሯል፡፡ አዎ ምርጫ ቦርድም ሆነ ኢህአዲግ በህግ የበላይነት ሊያምኑና ህግን ሊያከብሩ ብሎም በተሰጣቸው ገደብ መሰረት ሊንቀሳቀሱ ይገባል፡፡ ይህ ባልሆነበት ሁኔታ ዴሞክራሲ፣የህግ የበላይነት ….ወዘተ እያሉ መደስኮሩ ጉንጭ ከማልፋት በተዘለለ ለዜጎች ጠብ የሚልላቸው ነገር አይኖርም፡፡ መንግስታት አንባገነን በሆኑበት አግባብ ገለልተኛ ተቋማትን መገንባት አስቸጋሪ ነው፡፡ ….በሀገራችንም እየሆነ ያለው ይህ ሀቅ ነው፡፡ ምንም እንኳ የሀገሪቱ የይስሙላ ህገ መንግስት በአንቀፅ 102 1-2 ስለምርጫ ቦርድ ገለልተኛ ተቋምነት ቢደነግግም፤ እውነታው ግን ከዚህ ፍፁም ያፈነገጠና ምርጫ ቦርድ ገለልተኛ ለመሆን ቀርቶ የመንግስት ክንፍ ሆኖ በመስራት ላይ ይገኛል፡፡ ….እሺ ይኸንንም ይሁን ብለን እንቀበል፤…..ኢህአዲግ ያላከበረውን ህገ-መንግስትና የህግ ማእቀፍ ምርጫ ቦርድ ያከብራል ብለን አንጠብቅ፤…ነገር ግን ምርጫ ቦርድ ከአንድ ተቋም ነኝ ከሚል መዋቅር የማይጠበቅና እጅግ የወረደ ተግባር ሲሰራ እየተመለከትንበት ያለው ሁኔታ በጣም የሚያሳዝንና ተቋሙንም ሆነ የተቋሙ አመራሮችን ከታሪክ ተጠያቂነት የሚያድናቸው ሆኖ አናገኘውም፡፡

ምርጫ ቦርድ እንደተቋም ያስፈፅማቸውና ሊተገብራቸው ዘንድ የሚጠበቁ ተግባራት በህግ ተለይተው ተቀምጠውለት ሳለ በፓርቲዎች አሰራርና የውስጥ ጉዳይ እንደርጎ ዝንብ ጥልቅ እያለ፤በማያገባውና በህግም ሆነ በአሰራር በማይመለከተው ተግባር ውስጥ ህገ-ወጥ ተግባር መፈፀሙ ምናልባትም የሀገራችን ህግ ምን ያህል እንደወረደና የምርጫ ቦርድ ማንአለብኝነት ከኢህአዲግ የጀርባ እጅ ጋር መያያዙንና የህወሀት
/ኢህአዲግና/የምርጫ ቦርድን የአንድ ሳንቲም ሁለት ገፅታነት ቁልጭ አርጎ የሚያመላክት ነው፡፡
በህግ የበላይነት በሚያምኑ መሪዎችና ህዝቦች መካከል ፤…‹‹ህግ›› ማለት ልጓም ነው፡፡ አንድ ፈረስ በተፈቀደለት አቅጣጫና ፍጥነት በተገቢው ሁኔታ ይሄድ ዘንድ ልጓም ይበጅለታል፡፡ ልጓሙ ህግ ነው፤ ፈረሱ ከልጓም ከወጣ በሰውም ላይ ሆነ በራሱ ላይ አደጋ ሊያስከትል ይችላል፡፡ …..ልጓሙን ይዞ ፈረሱ ላይ ተግባራዊ የሚያደርገው ደግሞ የጋሪው አሽከርካሪ ነው፡፡ ስለዚህ ባለጋሪው ከፍተኛ ሀላፊነት አለበት ማለት ነው፡፡…..በህዝብም ላይ ተመሳሳይ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ህዝቦች በጋራ ተስማምተው ያወጡት ህገ-መንግስትና የየተቋማቱ ልዩ ልዩ ማስፈፀሚያ ህጎችና የህግ ማእቀፎች በሀገሪቱ ላይ ለሚደረገው ማንኛውም እንቅስቃሴና አሰራር ልክ እንደ ልጓሙ ሁሉ ገደብ አድርገውለታል፡፡ …..ከዚህ ልጓም የወጣ ደግሞ፤ …..ህገ-ወጥና የህግን የበላይነት የማያከብር ይባላል፡፡
በሀገራችን ያለው ሁኔታ በልጓም (በህግ) የበላይነት ማመን በወሬ ደረጃ ሆኖ የምናገኘው ኢህአዲግም ሆነ ሌሎች ተቋማት ህግንና አሰራርን በገሀድ ሲጥሱትና ተጠያቂ የሚሆኑበት አሰራር ሳይኖር ሲቀር ነው፡፡ …..ለነገሩ የሀገሪቱ መንግስት ነኝ ባይ ፓርቲ ህጉን እንዳሻው እየጣሰና እየረገጠ ባለበት ሁኔታ ሌሎች ተቋማትና ግለሰቦች ህጉን ቢጥሱ ምን ሊደንቀን ይገባል??? ……. ሰሞኑን እንደተከታተልነው ምርጫ ቦርድ ከተፈቀደለትና ከሚመለከተው ተግባር ውጭ በመውጣት በአንድነት ፓርቲ ላይ የጀመረው የውንብድናና የማንአለብኝነት ተግባር እጅግ አሳፋሪና የወረደ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ …….ምርጫ ቦርድ ‹‹ፅድቁ ቀርቶብኝ፣……›› እንደሚባለው ምንም እንኳ እንደአንድ ገለልተኛ ተቋም ለፓርቲዎች የሚጠበቅበትን ሀላፊነት ከአድሏዊነት በፀዳ መልኩ ማገልገል ቢሳነውም በማያገባው ሁሉ ጥልቅ እያለ የሚፈፅመው የህግ ጥሰትና የአሰራር ዝቅጠት ድርጊቱ ሆን ተብሎና በኢህአዲግ ተልእኮ አስፈፃሚነት የሚሰራ ትወና ለመሆኑ ማስረጃ ነው፡፡ …..ምርጫ ቦርድ በአንድነት ፓርቲ ላይ የከፈተው የተልእኮ ዘመቻ፤……. መላው ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ ሊያውቀውና ሊገነዘበው የሚገባ ታሪካዊ ስህተት ነው፡፡ ምርጫ ቦርድ እስካሁን በህዝብና በፓርቲዎች ላይ እየፈፀመ ያለው ደባ እንዳለ ሆኖ ልጓሙን የበጠሰው ይህ ተቋም በቀጣይነት ለፓርቲዎች ህግ ላውጣ፤ የፋይናንስ ጉዳያችሁን ላስተዳድር፤የዲሲፕሊንና ሌሎች የፓርቲው እርምጃ በኔ በኩል ይፈፀም፤…ለኢህአዲግ መስገድ በኔ በኩል የሚፈፀም የፓርቲዎች ግዴታ ነው፤የየፓርቲዎችን ፕሬዝዳንት በኢህአዲግ መልማይነት በእኔ አፅዳቂነት ይፈፀም ……. ወዘተ የሚሉ ወራዳና የወረዱ ተግባራትን እንደሚፈፅም አልጠራጠርም፡፡ይህ ተቋም በህዝብ ላይ ለፈፀመው ደባና ንቀት ተጠያቂ የሚሆንበት ቀን እሩቅ አይሆንም፡፡ …..አንድነት ፓርቲና ሌሎች የምርጫ ቦርድ መረን ለቀቅ ድርጊት ሰለባ የሆኑ ፓርቲዎች ግን የህዝብን አደራ ተሸክመው፤በዚህ ተልካሻና የማይከበር ተቋም ሴራ ከትግሉ መራቅ እንዴሌለባቸው የሚታመን በመሆኑ፤…… በተባበረ ክንድ የምርጫ ቦርድንም ሆነ የኢህአዲግን ውጥን የሚያከሽፍ የትግል ስልት ነድፈው እንደሚንቀሳቀሱ አልጠራጠርም፡፡ ….ምናልባት ፓርቲዎች ባመጡት ጠንቅ ሳይሆን በኢህአዲግና ምርጫ ቦርድ ሴራ ትግሉ ደም የሚያቃባና በመስዋትነት የታጀበ ሊሆን ይችላል፤ ነገር ግን ለዚህ ደም መፋሰስ ተጠያቂዎቹ ኢህአዲግና ምርጫ ቦርድ መሆናቸውን መላው ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ ሊረዳው የሚገባ ሀቅ ነው፡፡ …….አመሰግናለሁ!!! …….አንብበው ሲጨርሱ ሼር ማድረግዎትን አይርሱ!!! …..ድል የህዝብ ነው!!!

Wednesday, January 14, 2015

ከምርጫው በፊት ምርጫ ቦርድ የሚደክምለት አብዩት፤ – ከዳዊት ሰለሞን


አቦጊዳ  
በእርግጥ ምርጫ ቦርድን ለፕሮፌሰር መርጋ በቃና በመስጠት ኢህአዴግን ከጨዋታው ውጪ ማድረግ አይቻልም፡፡ የኢህአዴግ የስልጣን ደም ስር በዚህ ተቋም የተተበተበ በመሆኑ ምርጫ ቦርድን እንደ አንድ ራሱን የቻለ ነጻ ተቋም መቁጠር እንኳን ለእኛ ለኢትዮጵያዊያኑ ቀርቶ ለምዕራባዊያኑም የሚዋጥ አይሆንም፡፡ሁለቱ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች መሆናቸውን ለማሳየት ብዙ ርቀት መጓዝ አይጠበቅም፡፡
በአገሪቱ የተከናወኑ አገር አቀፍና ክልላዊ ምርጫዎች ለሁለቱ ተጋምዶ አይነተኛ ማሳያዎች ናቸው፡፡በኢህአዴግ ኮሮጆ ገልባጭነት ለተደረጉ የምርጫ ማጭበርበሮች ምርጫ ቦርድ ህጋዊነትን እያጎናጸፈ የህዝብ ልጆች ደም በየዓምስት ዓመቱ እንደ ጎርፍ እየወረደ ኢህአዴግ የስልጣን ኮርቻውን እንደተፈናጠጠ አራት ኪሎ ይገኛል፡፡
ለስድስተኛ ጊዜ የሚደረገው አገር አቀፍ ምርጫ ከሶስት ያነሱ የወራት ዕድሜዎች ብቻ ቀርተውታል፡፡ምርጫ ቦርድ የህዝብ ታዛቢዎችን በማስመረጥ የመራጮች የምዝገባ ወረቀት መታደል መጀመሩን ቢገልጽም በገዢውና በተፎካካሪ ፓርቲዎች መካከል ፉክክሩን ክፍት ሊያደርጉ በሚችሉ ጉዳዩች ዙሪያ የመነጋገር ምልክት አይታይም፡፡
ከሁሉ በከፋ መልኩ ምርጫ ቦርድ ድግሱ እንደደረሰለት ቅን ደጋሽ በአምስት ዓመት አንድ ግዜ የሚያገኘውን ዕድል በቻለው መጠን ክፍት፣ነጻና ሁሉን አሳታፊ ማድረግ ሲገባው ለገዢው ቡድን ያለው አጋርነት አቅሉን አስቶት ድግሱን ሊያደምቁ በሚችሉ ፓርቲዎች ላይ የማስፈራሪያ መግለጫዎችን በማስደመጥ ተወጥሯል፡፡
በቀጣዩ ምርጫ የተሻለ ውጤት ለማግኘት ከብዙ ማደናቀፊያዎች ጋር እየታገለ እዚህ የደረሰውን አንድነትን ምርጫ ቦርድ ሰንካላ ምክንያቶችን በማቅረብ በአጭር ግዜ ውስጥ ተደጋጋሚ ጠቅላላ ጉባኤዎችን እንዲያከናውን አስገድዶታል፡፡እውነቱን ለመናገር ምርጫ ቦርድ ጠቅላላ ጉባኤ አድርገዋል በማለት የእውቅና ሰርተፊኬት ከሰጣቸው ፓርቲዎች ውስጥ ምን ያህሉ ጠቅላላ ጉባኤ አድርገዋል ?ኦዲት ተደርገዋል?ምን ያህሉ አድራሻ አላቸው ?የአባላት ቁጥራቸው ስንት ነው?ስንቶቹስ ፕሬዘዳንት(ሊቀመንበር)ምክትል ፕሬዘዳንት ጸሀፊና የህዝብ ግኑኝነት አላቸው?ለምሳሌ የአየለ ጫሚሶን ቅንጅትን እንውሰድ አቶ አየለ የፓርቲው ሊቀ መንበር፣ ዋና ጸሐፊና ገንዘብ ያዥ ሲሆኑ የተረከበውን ህገ ወጥ አጠና ደብቆ በመሸጡ ከፖሊስነቱ የተቀነሰው አቶ ሳሳሁልህ የፓርቲው ምክትል ፕሬዘዳንት፣ የህዝብ ግኑኝነትና የሚዲያ ክፍል ሀላፊ ነው፡፡ ቅንጅት የሁለቱ ሰዎች ንብረት ቢሆንም ምርጫ ቦርድ የጠቅላላ ጉባኤ፣የኦዲትና የስልጣን ክፍፍልን የሚመለከት ጥያቄ አቅርቦ አያውቅም ከዚህ ይልቅ እነሳሳሁልህ ከምርጫ ቦርድ የተሳትፎም ይሁን የእውቅና ደብዳቤ በማግኘት ተወዳዳሪ የላቸውም፡፡
ምርጫ ቦርድ በኪሳቸው ማህተማቸውን ይዘው ለሚዞሩ የፓርቲ አመራሮች ያልተደረጉ ጠቅላላ ጉባኤዎችን እንደተደረጉ በመውሰድ የእውቅና ሰርተፊኬት የአመራሮቹ መኖሪያ ቤት ድረስ በፖስተኛ እንደሚልክ ለሚያውቅ ሰው አሁን ደርሶ አንድነትን ሱሪ በአንገት ማለቱ አይደንቀውም፡፡
እነ መርጋ እነዚህን ፓርቲዎች የህልውናቸው ማረጋገጫ በመሆናቸው ይፈልጓቸዋል፡፡ፓርቲዎቹ በእነ መርጋ ድግስ እየተካፈሉ ኢህአዴግ ቢያንስ ምዕራባዊያንን የሚሞግትበትና የዋህንን የሚያስትበትን በር ይከፍቱለታልና ለመኖራቸው፣ለመዋለዳቸው ተግቶ ይሰራል፡፡በአንጻሩ ኢህአዴግ ፖሊሲ የሚቀርጽ፣ስትራቴጂ የሚነድፍ፣ፕሮግራም የሚያወጣ፣አባላቱን ለማብዛት በመላ አገሪቱ እግሩን ለመትከል የሚታትር እንደ አንድነት ያለ ፓርቲ ወደ ጨዋታው ሜዳ እንዲገባ አይፈቅድም፡፡ እናም መርጋ መጋረጃውን ገልጠው ለኢህአዴግ ዘራፍ ይሉለታል፡፡ኢህአዴግ ድምጹን አጥፍቶ ክርክሩ በምርጫ ቦርድና በፓርቲዎች መካከል እንደሆነ እስክናምን ድረስ መገኘውን ይሰውራል፡፡መርጋን ብትለቃቸው አንተን አያድርገኝ ካላቸው ወራቶች ተቆጥረዋል፡፡
አብዩት የሚጠራው ማን ነው?ምርጫ ቦርድ ለምርጫ እየተዘጋጀ የሚገኝ ከመሰለን ተሞኝተናል፡፡ሰሞነኛው ድርጊቱ አብዩትን እያገለገለ ለመሆኑ አስረጂ ነው፡፡በመላ አገሪቱ እየተንቀሳቀሰ የሚገኘውን አንድነትን ከምርጫው ለማገድ ከጫፍ ደርሷል፡፡ፓርቲው ህገ ወጥ ምርጫ አድርጓል ላሉ ሰዎች በሆቴል ውስጥ ምርጫ እንዲያከናውኑ ሁኔታዎችን በማመቻቸት መሪዎችን እንዲመርጡ አስደርጓል፡፡ይህም ምርጫ ቦርድ አንድነትን በበላይ ፈቃዱ ለሚመራው ካቢኔ ከመስጠት ይልቅ ትዕግስቱ አወሉን መረጥን ላለው ቡድን ለመስጠት መዘጋጀቱን ያሳያል፡፡በበላይ የሚመራውና የብሄራዊ ምክር ቤቱን እውቅና ያገኘው ቡድን ከአፈንጋጩ ቡድን ጋር እንዲጋጭ በምርጫ ቦርድ ብዙ ተለፍቶለት የነበረ ቢሆንም ትግሉን ከገዢው ቡድን ጋር ማድረጉ ሊሰራ ለነበረው ድራማ ግብዓት አሳጥቶታል፡፡
ምርጫ ቦርድን ወረቀት ላይ እንደቀረ ኪሳራ እንደሚቆጥረው የተናገረው የአንድነቱ ፕሬዘዳንት በላይ ፓርቲው የዘንድሮውን ምርጫ የሞት ሽረት ትግል አድርጎ መውሰዱን ይፋ አድርጓል፡፡ምርጫ ቦርድ ይህንን ሀይል በፈራው ኢህአዴግ በመታዘዙም አንድነት የሌለበትን ምርጫ ለማዘጋጀት የወሰነ ይመስላል፡፡
አንድነቶች ምርጫውን ታሳቢ በማድረግ ሲሰሩ በመቆየታቸው ወደ ምርጫ አትገቡም የሚለው ውሳኔ ብዙ ሊያሳዝናቸው ይችላል፡፡የምርጫ ፓርቲ መስርተው ለሚታገሉ ቡድኖች ምርጫ አትገቡም ሲባሉ የሚኖራቸው አማራጭ ሁለት ብቻ ነው፡፡ከምርጫ ቦርድ ያገኙትን ሰርተፊኬት በመመለስ ወደየቤታቸው መበታተን ወይም ህዝባዊ እምቢተኝነት በስርዓቱ ላይ እንዲፈጠር መስራት፡፡አንድነቶች የመጀመሪያውን አማራጭ ከዚህ ቀደም ጠረጴዛቸው ላይ በማቅረብ ውድቅ ያደረጉት በመሆኑ የሚተገብሩት ሁለተኛውን አማራጭ ይሆናል፡፡
ለህዝባዊ እምቢተኝነቱ ህዝብ ትልቁ መሳሪያ መሆኑ አይካድም፡፡አንድነት ይህንን ህዝብ ማግኘት እንደማያስቸግረው ከወዲሁ መገመት ይቻላል፡፡በስርዓቱ የተከፉ ኢትዮጵያዊያን ቁጥር የትየሌለ ነው፡፡ስርዓቱ ያልነካው አንገቱን እንዲደፋ ያላደረገው የህብረተሰብ ክፍል የለም፡፡ደደቢት በረሃ ድረስ ያመራችው አርቲስት ሳትቀር ለስርዓቱ ጉምቱዎች ‹‹እናንተስ በምርጫ ትወርዳላችሁን››በማለት ጠይቃቸዋለች፡፡አርቲስቷ ያነሳችው ጥያቄ የእርሷ ብቻ አለመሆኑም ሊሰመርበት ይገባል፡፡ ይህ ለውጥ ሊታይበት የሚችለው ሰላማዊ መንገድ ዝግ ሲሆን የሚከፈተው የአብዩት መንገድ በመሆኑ በመንገዱ ኢህአዴግን ለማሳለፍ ከአንድነት ጎን የህዝብ ጅረት ሊሰለፍ ይችላል፡፡
የአንድነት መታገድ የአንድነት ብቻ አይሆንም
ምርጫ ቦርድ በአቋሙ በመጽናት ይህንኑ ካደረገ በአንድነት ላይ የተወሰደው እርምጃ ህገ ወጥነት ተሰምቷቸው የተወሰኑ ፓርቲዎች ከምርጫው ራሳቸውን ሊያገሉ ይችላሉ፡፡መድረክ ከአንድነት ጋር በመፋታቱ የአንድነትን ከምርጫ መታገድ ከቁብ ቆጥሮት እኔም ከምርጫው እወጣለሁ ይላል በማለት ለመናገር ባልደፍርም ሰማያዊ ና መኢአድ ራሳቸውን ሊያገሉ ይችላሉ፡፡ይህም ስርዓቱ ላይ የሚታይ ጫናና ህዝባዊ እምቢተኝነትን ከምርጫው በፊት ለመፍጠር ዕድል ይከፍታል፡፡አብዩቱ የሚፈጠረው ግን በምርጫ ቦርድ ወገንተኛ ውሳኔ እንጂ በፓርቲዎቹ አለመሆኑ መታወቅ ይኖርበታል፡፡ፓርቲዎቹማ በምርጫው ለመሳተፍ ራሳቸውን እያዘጋጁ የነበሩ ናቸው፡፡10346525_435976806552557_6872474233828421189_n
10428627_759966307421639_3753389504227116176_n
64334_759966300754973_6395978200166176093_n

በዞን 9 ጦማርያንና ጋዜጠኞች ላይ የቀረበው ክስ በድጋሜ ‹‹ተሻሻለ››

ዘሐ በ ሻ 

  • 180
     
    Share
በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር
ጦማርያኑና ጋዜጠኞቹ ጥር 6 ቀን 2007 ዓ.ም ለ15ኛ ጊዜ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ቀርበዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ የተሰየመው ቀደም ብሎ በጦማርያኑ እና ጋዜጠኞች ላይ የተመሰረተው ክስ እንዲሻሻል ባዘዘው መሰረት የፌደራል አቃቤ ህግ ክሱን ፍርድ ቤቱ በሰጠው ትዕዛዝ መሰረት ያላሻሻላቸው ነጥቦች ስለነበሩ እነዚህኑ ነጥቦች በድጋሜ አሻሽሎ እንዲቀርብ ባዘዘው መሰረት የተሻሻለውን ክስ ለመስማት ነበር፡፡
36884-zone9-bloggers4
በመሆኑም የፌደራል አቃቤ ህግ አሻሽየዋለሁ ያለውን ክስ ይዞ ቀርቧል፡፡ ክሱ ‹‹ሌሎች ብዙ ‹ኬዞች› ስላሉ›› በሚል ምክንያት በችሎቱ ላይ በንባብ እንዲሰማ አልተደረገም፡፡ ተሻሻለ የተባለው ክስ ለተከሳሾችና ለጠበቆች እንዲደርስ የተደረገውም እዚያው ችሎት ውስጥ ነው፡፡
ክሱ በንባብ ባለመሰማቱና ጠበቆቹና ዳኞቹም ስላላነበቡት በሚል ተሻሻለ በተባለው ክስ ላይ ምንም አስተያየት አልቀረበም፡፡ በመሆኑም ክሱ መሻሻል አለመሻሻሉን ለመመርመርና ብይን ለመስጠት ለጥር 20 ቀን 2007 ዓ.ም ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡
የጦማርያኑ እና ጋዜጠኞች ጠበቃ የሆኑት አቶ አምሃ መኮንን እንዳሉት በቀጣዩ ቀጠሮ ላይ ፍርድ ቤቱ በሰጠው ትዕዛዝ መሰረት ተሻሽሎ ካልሆነ ነጥቦቹን ፍርድ ቤቱ ውድቅ ያደርጋል ብለው እንደሚጠብቁ ገልጸዋል፡፡ ‹‹በእኛ በኩል ከዚህ በኋላ የማሻሻያ ሀሳብ አቅርበን ጊዜ አንፈጅም፤ ከሚቀጥለው የፍርድ ቤቱ ውሳኔ በኋላ መደበኛ ክርክራችንን መቀጠል ነው የምንፈልገው›› ሲሉም አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
በዛሬው የችሎት ውሎ ላይ በጣም ብዙ እስረኛ (ተከሳሽ) ችሎቱ ውስጥ በመገኘቱ ምክንያት ከፍተኛ የቦታ ጥበት ማጋጠሙ ተስተውሏል፡፡ በአጠቃላይ እስከ 70 የሚደርሱ እስረኞች በችሎቱ ተገኝተዋል፡፡ ስለሆነም ችሎቱን መታደም የቻሉት ጥቂት ጋዜጠኞችና ዲፕሎማቶች ብቻ ሆነዋል፡፡ የተከሳሽ ቤተሰብና ወዳጅ ዘመዶች ችሎቱን መታደም አልቻሉም፡፡

አንዳርጋቸው ጸጌ በህወሀት የሸፍጥ የምርመራ ወጥመድ ውስጥ



ዘሐ በ ሻ 

  • 560
     
    Share
ከፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም ትርጉም በነጻነት ለሀገሬ
አንዳርጋቸው ጽጌ በህወሀት ወንድሞች ቡድናዊ የሸፍጥ ከበባ ስር
 ቮልቴር (ፍራንኮይስ ማሬ አሮት) እንዲህ በሚለው ምልከታቸው በስፋት ይታወቃሉ፣ “አንድ ሰው ከሚሰጣቸው ምላሾች ይልቅ በሚያቀርባቸው ጥያቄዎች ምንነቱ ይገመገማል፡፡“
ቮልቴር ብልህነትን በተላበሰ መልኩ እንዲህ የሚል ምልከታም በተጨማሪ አካሂደዋል፣ “ጥሩንባቸውን እየነፉ እጅግ ብዛት ያለውን ህዝብ ካስጨረሱ ገዳዮች በስተቀር ሁሉም ህይወትን ያጠፉ ነብሰ ገዳዮች ይቀጣሉ፡፡“ ይኸ ነገር እንዴት ያለ እውነታ ነው እባካችሁ! አሁን በህይወት የሌለው መለስ ዜናዊ እና እራሱን ህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ (ህወሀት) እያለ የሚጠራው የወሮበላ ቡድን በሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን/ት ወገኖቻችንን በመግደል ከምዕራቡ ዓለም የሚደረግላቸውን እርዳታ በመቀበል ፌሽታ እና ደስታ በማድረግ ከህዝብ እልቂት ሰይጣናዊ ወንጀሎቻቸው ለማምለጥ ላይ ታች በማለት በመንፈራገጥ ላይ ይገኛሉ፡፡
ባለፈው ሳምንት በአንዳርጋቸው ጽጌ ተሰጠ የተባለ የ10 ደቂቃ ከ31 ሰከንዶች ቆይታ ያለውን ሁለተኛ ጊዜ የቀረበ የሙያ ሳይሆን የልምምድ ድራማቸውን በህዝብ ግብር በሚተዳደረው ቴሌቪዥን በማይታዩ ጥያቄ አቅራቢ መርማሪዎች እና ሰዎች የእራሳቸውን የህሊና ዳኝነት እንዲሰጡ በሚጋብዝ መልኩ የተቀነጫጨበ እና በውል ለመረዳት የማይቻለውን ምላሽ የተባለውን ቃለ ተውኔት እንደሰጡ አድርገው አቅርበው ነበር፡፡
andargachew Tsegeበኢትዮጵያ ባለው አገዛዝ የተቃዋሚ ቡድን ከሆነው እራሱን የግንቦት ሰባት ንቅናቄ ለፍትህ፣ ለነጻነት እና ለዴሞክራሲ እያለ የሚጠራውን ድርጅት ዋና ጸሀፊ የሆኑትን አንዳርጋቸው ጽጌን እ.ኤ.አ ጁላይ 2014 በየመን ካለው ገዥ አካል ጋር የሸፍጥ ዱለታ በማድረግ በተሳካ ሁኔታ ወደር የማይገኝለትን ጠለፋ አካሂደው ነበር፡፡ እ.ኤ.አ በ2009 እና በ2012 አንዳርጋቸው በሌሉበት አሸባሪ በሚል የሸፍጥ ውንጀላ በህወሀት ክስ ተመስርቶባቸው በዝንጆሮው የይስሙላ ፍርድ ቤት የሞት ቅጣት ተበይኖባቸው ነበር፡፡
የአቶ አንዳርጋቸውን አሳፋሪ እና ህገወጥ ጠለፋ በማስመልከት “ኢትዮጵያ፡ ልዩ የሆነ የወንጀል ትወና“ በሚል ርዕስ እኩይ ድርጊት መሆኑን በሳምንታዊ ጦማሬ ላይ አውግዠ ነበር፡፡
አንዳርጋቸው የእንግሊዝ ዜግነት ያላቸው ሲሆኑ በትውልዳቸው ኢትዮጵያዊ ናቸው፡፡ ሆኖም ግን በጣም የሚያሳፍረው ነገር የእንግሊዝ ዜግነታቸው ለስም ብቻ የመሆኑ ጉዳይ ነው፡፡ አንዳርጋቸው ከእስር ቤት እንዲፈቱ የእንግሊዝ መንግስት ምንም ያደረገው ነገር ወይም ደግሞ በአስከፊነቱ በዓለም ታዋቂ ከሆነው የመለስ ዜናዊ እስር ቤት የሰብአዊ መብት ረገጣ እና ስቃይ ነጻ እንዲሆኑ የሰራው ስራ የለም፡፡ የህወሀት ወንድሞች ከስድስት ወራት በላይ አንዳርጋቸው ጽጌን ለተደጋጋሚ ጊዜ የብዙሀን መገናኛ የመድረክ የቅጥፈት ተውኔት ማሳያ ሲያደርጓቸው የእንግሊዝ መንግስት አንድም ዓይነት የወሰደው እርምጃ የለም፡፡
እ.ኤ.አ በ1963 በጸደቀው የኮንሱላር ግንኙነት የቬና ስምምነት መሰረት የእንግሊዝ መንግስት ፍጹም በሆነ መልክ ግዴታውን መወጣት አልቻለም፡፡ የእንግሊዝ መንግስት በውጭ የሚኖሩ ዜጎቹን ደህንነት በመጠበቁ እና እገዛ በሚጠይቁ ዜጎቹ ጉዳይ ላይ በሁለት ቢላዋ ምላሱ በማውራት ላይ ይገኛል፡፡ የእንግሊዝ ባለስልጣኖች እንዲህ ይላሉ፣ “በኮንሱላር ባለስጣኖቻችን ወይንም ደግሞ የዲፕሎማሲ ባለስልጣኖቻችን አማካይነት በውጭ ሀገር በችግር ላይ ለሚገኙ ዜጎቻችን የምንሰጠው እገዛ የውጭ ፖሊሲያችን የመሰረት ድንጋይ ነው፡፡“ ከዚህም በተጨማሪ የኮንሱላር እገዛ የእንግሊዝ ዜጎች ማግኘት ያለባቸው የህግ መብት አይደለም በማለት እንዲህ ይላሉ፣ “የእንግሊዝ መንግስት ለዜጎቹ የኮንሱላር እገዛ ለመስጠት ወይም ደግሞ የዲፕሎማሲ ጥበቃ ለማድረግ በሀገር ውስጥም ሆነ በዓለም አቀፍ ህጎች ግዴታ የለበትም፡፡“ ከዚህም በላይ በውጭ የሚገኙ ዜጎቻቸው የማሰቃየት ድርጊት እንዳይፈጸምባቸው ወይም ሊፈጸምባቸው እንዳይችል ለማድረግ የዜጎቻቸውን ደህንነት ለመጠበቅ የእንግሊዝ መንግስት የጸረ ማሰቃየት ስትራቴጅ አንዱ እና ዋና ተግባሩ ነው፡፡ የእንግሊዝ ንጉሳዊ ቡድን ጸሀፊ፣ ገጣሚ እና ወታደር የነበሩት ጌታ ዋልተር ራለህ ተገቢ በሆነ መልኩ እንዲህ የሚል ጥቆማ አድርገው ነበር፣ “ኦ፣ የማታለል ተግባራትን ስንፈጽም በነበረበት ጊዜ ምን ዓይነት ድር ማድራት እንደጀመርን!“
የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ ቢሮ አንዳርጋቸው ጽጌ በወያኔ የዝንጀሮው የይስሙላ ፍርድ ቤት ሁለት ጊዜ የሞት ፍርድ የተበየነባቸው መሆኑን እና ከፍተኛ የሆነ ማሰቃየት እንደተፈጸመባቸው ከምንም ጥርጣሬ በላይ አሳምሮ ያውቃል፡፡ እስከ አሁን ድረስ በእንግሊዝ መንግስት የተደረገው ጸጸትን መግለጽ እና ከየመን ባለስልጣኖች ዘንድ ተደጋጋሚ የሆኑ መረጃዎችን መጠየቅ፣ ስለአንዳርጋቸው የእስር ሁኔታ ከቬና ስምምነት በተጻረረ መልኩ መረጃ ማግኘት ያለመቻል ችግር እንዲሁም አንዳርጋቸው ጽጌ በኢትዮጵያ የሞት ብይን ፍርድ እንዳይሰጥባቸው ለማድረግ ግልጽነት የጎዳላቸው አራምባ እና ቆቦ የሆኑ የማስመሰያ መግለጫዎችን ማውጣት እና ጉዳዩ አሳስቦናል የማለት የይስሙላ ጥረት ነበር፡፡ እንደ አንድ ዘገባ ከሆነ ሚስተር ሲሞንድስ የተባሉ አፍሪካዊ ሚኒስትር የኢትዮጵያ ባለስልጣኖች የኮንሱላር ተደራሽነትን የማይገልጹ በመሆናቸው ሚኒስትሩ የተሰማቸውን ጥልቅ ስሜት ገልጸው ነበር፡፡
አሜሪካኖች እንደሚሉት “ልዩ የሆነ የዳክዬ የደስታ ጩኸት ነው!” ሆድ ሲአቅ ዶሮ ማታ ይላል ያገሬ ሰው። በእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት በኩል መልካም የሆነ የአዞ እንባ የማንባት የታዕይታ ተውኔት ነው፡፡ የእንግሊዝ ሀገር ዜጎችን ደህንነት በመጠበቅ ሁኔታ ላይ አንደኛ እና ሁለተኛ ደረጃ ዜጋ ይኑር አይኑር እንዲሁ የማሰቃየት ስራ ቢሰራ እና ሁለት ምላስ ንግግር ቢደረግ ኖሮ የሚያስደንቀኝ ነገር አይኖርም ነበር፡፡ አሁን ጊዜ ማጥፋቱን ልተው እና ተገቢውን ጥያቄ ላቅርብ፡፡ በኢትዮጵያ ወሮበሎች እየተሰቃዩ ያሉትን አንዳርጋቸውን የሀገሩ (የንግሊዝ) ሁለተኛ ዜጋ የሆኑትን ግለሰብ መብት ለማስከበር እና ከማጎሪያው እስር ቤት እንዲለቀቁ ለማድረግ የእንግሊዝ መንግስት ምን ያደረገው ነገር አለ? በጭራሽ ምንም ያደረገው ነገር የለም!
ያም ሆነ ይህ ወደ ወያኔ እና ስለአንዳርጋቸው የብዙሀን መገናኛ የመድረክ ላይ ተውኔት እንመለስ፡፡
እውነታውን ተመርኩዘን ስለአንዳርጋቸው ሁኔታ የህሊና ዳኝነት እንድንሰጥ በቪዲዮ ቁራጭ (ክሊፕ) በግልጽ የቀረበውን የወያኔ ግብዣ ተቀብየዋለሁ፡፡ እኔን የገረመኝ እና ከሁሉም በላይ ያስደንቀኝ ነገር በተቃራኒ መልኩ እነዚህ ህሊና የሚባል ነገርጨርሶ ያልፈጠረባቸው ህሊናቢስ የሸፍጥ ስብስቦችለህሊና ዳኝነት በማለት ጥያቄ የማቅረባቸው ጉዳይ ነው፡፡ የሌባ አይነደርቅመልሶ ልብ አድርቅ ይላል ያገሬ ሰው። ሆኖም ግን ላልተገለጹ ጥያቄዎች፣ በማይታወቅ ቦታ እና ጊዜ ለስምየለሽ እና ማንነቱ ላልታወቀ መርማሪ ስለሰጡት ምላሽ እንዴት አድርጌ ነው በአንዳርጋቸው ላይ የህሊና ፍርድ መስጠት የምችለው!?
ፍትሀዊነት በጎደለው እና በአስከፊ የውሸት የተውኔት መድረክ ላይ ለመታየት አንድ ሰው የውንጀላ ክስ የሚመሰረትበት እና በሚሰጣቸው ምላሾች ብቻ የሚዳኘው በእስፓኝ ሀገር በመካከለኛው የዘመን (የዛሬ አምስት መቶ ዓመት በፊት) አቆጣጠር ጊዜ ብቻ ነበር፡፡ (በእርግጥ በሶቪየት ውስጥ በስታሊን የአገዛዝ ዘመን እንደተደረገው ሁሉ የናዚ ወንጀለኞችም በተመሳሳይ መልኩ አንድ ሰው በታዕይታው የፍርድ ሂደታቸው አንድ ሰው በሰጠው ምላሽ ላይ ብቻ በመመርኮዝ ብያኒያቸውን ይሰጡ ነበር፡፡) በእኔ አስተያየት በ10 ደቂቃ ከ31 ሰከንዶች በፈጀው የቪዲዮ እይታ በአቶ አንዳርጋቸው ላይ ወያኔ ያደረገው የመድረክ ላይ ተውኔት በእርግጥም በመካከለኛው ዘመን የተደረገውን ፍትሀዊነት የጎደለውን እና አስከፊውን የመድረክ ላይ ተውኔት ይመስል ነበር፡፡ ይህ ፍትሀዊነት የጎደለው እና አስከፊ የመድረክ ላይ ትወና ከአንድ ሺህ የተለያዩ ጥያቄዎች ውስጥ አንድ ትክክለኛ መልስ ብቻን ለማግኘት ከተለመደው እምነት እና አስተሳሰብ ውጭ ዓላማ አድርገው የተነሱ ናቸው፡፡ የኸውም “የነበረኝን ጽኑ እምነት ቀይሪያለሁ፣ ተገልብጫለሁ”! የሚል መልስ ብቻ ትክክለኛው እንደሆነ በቅጥፈት ማሳያ የትወና መድረክ ላይ እንዲታይ ማድረግ ነው፡፡
ፍትሀዊነት የጎደለው እና አስከፊው የመድረክ ላይ ተውኔት በሀሰት ውንጀላ የቀረቡ ተጠርጣሪዎች ከተለመደው ባህሪያቸው እምነት ውጭ ለመናገር የሚፈሩ ከሆነ እና ሌሎችም እነርሱ የሚያውቋቸው እንደዚህ ያለ ጸባይ ያላቸው የሚጠረጠሩ ሰዎች ካሉ ይህንን በመተው እራሳቸውን ማውገዝ በሚለው ሂደቱ ይጀመራል፡፡ ያ እንግዲህ ይፋ በሆነ መልኩ እራስን ማውገዝ (እራስን መክሰስ) እና ተጠርጣሪው በመከላከል እስር ቤት ውስጥ በሚቆይባቸው ረዥም ጊዚያት የሚፈጸም ሂደት ነው፡፡ ፍትሀዊነት የጎደለው እና አስከፊው የመድረክ ላይ ተውኔት ሂደቶች በሚስጥር የሚካሄዱ ናቸው፡፡ ክስ የተመሰረተበት ሰው ለበርካታ ዓመታት በእስር ቤት ሲማቅቅ የቆየ ቢሆንም እንኳ ህጋዊ የሆነ የክስ መጥሪያ እንዲደርሰው አይደረግም ወይም ደግሞ የክስ መጥሪያው በማስታወቂያ እንዲለጠፍ አይደርግም፡፡ የተጠረጠሩ ፍትሀዊነት የጎደለው እና አስከፊ የመድረክ ላይ ተውኔት የሚፈጸምባቸው ዜጎች እራሳቸውን እንዲያወግዙ በሚገደዱበት እና ምርመራ በሚካሄድበት ወቅት በአንድ ክፍል ውስጥ ከቤተሰቦቻቸው እና ከጓደኞቻቸው ጋር መገናኘት እንዳይችሉ ሆነው ለብቻቸው እንዲታሰሩ ይደረጋል፡፡ ፍትሀዊነት የጎደለው እና አስከፊ የመድረክ ላይ ተውኔት በሚሰራበት ጊዜ የሂደቱ ስርዓት ልዩ ልዩ የማሰቃያ ዘዴዎችን በመጠቀም እንዲያምን የሚጠበቀው በሀሰት ውንጀላ በእስር ቤት የሚገኘው አማኝ በአሳማኙ ፈቃድ ብቻ እንዲያምን የሚያስገድድ የህግ መርህ አለው፡፡ በሀሰት ውንጀላ ተጠርጥሮ የተያዘው ግለሰብ እራሱ የሚያምነበትን እምነት ክዶ ከአሳማኙ በቀረበለት ሀሳብ መሰረት እራሱን አውግዞ እንዲናገር በማድረግ ይህንን የመድረክ ላይ ትወና ለህዝብ ፍጆታ ግብር እየከፈለ በሚያስተዳድረው ብዙሀን መገናኛ ላይ ፍትሀዊነት የጎደለው እና አስከፊው የመድረክ ላይ ተውኔት ለህዝብ ዕይታ እንዲቀርብ ከተደረገ በኋላ ወዲያውኑ እነርሱ የሚፈልጉትን ፍርድ በመስጠት በሀሰት በተወነጀለው ግለሰብ ላይ ይጭኑበታል፡፡
እውን በእውነት ወያኔ በቪዲዮ ቀርጾ አንዳርጋቸው ጽጌ የእራሳቸውን፣ የጓደኞቻቸውን እና የሌሎችን እምነት በማውገዝ የሰጡት መረጃ ወይም ምላሾች ናቸው ብሎ ያቀረባቸው ተራ ቅጥፈቶች የእርሳቸውን የጽናት አቋም እና እምነት በማንጸባረቅ የእርሳቸውን ምንነት ይገልጻሉን? የቪዲዮ ማስረጃው ወያኔ አንዳርጋቸውን ከሚያወግዝበት ውግዘት ጋር እኩል የውግዘት እንደምታ አላቸውን? የቪዲዮ ቀረጻው የወያኔን ፍትሀዊነት የጎደለውን እና አስከፊውን የመድረክ ላይ ተውኔት መሰረት በማድረግ ለፍርድ አሰጣጥ ሂደቱ በማስረጃነት ለመጠቀም ነውን? በድብቅ ለወያኔ የይስሙላው ፍርድ ቤት የተሰጠውን የአንዳርጋቸውን የቪዲዮ ማስረጃ መሰረት አድርገን የህሊና ፍርድ እንድንሰጥ እየተጋበዝን ነው ያለነው? የቪዲዮ ቀረጻ ማስረጃው አንዳርጋቸው ጽጌ በይፋ በህዝብ ፊት የወያኔን የወሮበላነት መርህ አሜን ብለው ተቀበሉ ብለን እንድናምን ነው የተፈለገው? የቪዲዮ ቀረጻ ማስረጃው በእርግጥ አንዳርጋቸው “ወደ ወያኔ ወሮበልነት ተቀይሪያለሁ” ብለው በእራሳቸው የስብዕና አንደበት አምነው የተናገሩት መሆኑን ያሰየናል? ወይም ደግሞ የቪዲዮ ቀረጻ ማስረጃው ወያኔ በአቶ አንዳርጋቸው ላይ ከዚህ ቀደም እንደበየነው አሁን ደግሞ ለሁለተኛ ጊዜ የሚያሳልፈውን የሞት ቅጣት የመጨረሻ ውሳኔ እና መግለጫ አስቀድሞ ለማሳየት ነውን?
አንዳርጋቸው ከቤተሰብ እና ከጓደኞቻቸው ጋር ፍጹም መገናኘት እንዳይችሉ የተደረገው ለምንድን ነው? አንዳርጋቸው ምንም ዓይነት ክስ ሳይደርሳቸው በጣም ለተራዘመ ጊዜ በእስር ቤት ውስጥ እንዲቆዩ ከተለመደው እምነት ውጭ የሆነውን እምነታቸውን አብዮታዊ ዴሞክራሲን (ምንም ምን ይሁን) ተቀብለዋል በማለት በድብቅ ይዞ ለማቆየት ወይም ደግሞ ከዚህ በፊት እንደገለጽኩት ሁሉ የመለሳውያንን/ትን የጨለማ መንገድ በማለት ሲያራምዱት የቆዩትን እምነታቸውን እርግፍ አድርገው ጥለውታል ለማለት ነው? የኢትዮጵያ ህገ መንግስት አንቀጽ 21 (2) የሚከተለውን መብት ያጎናጽፋል፡ “ማንኛውም በህግ ከለላ በቁጥጥር ስር ያለ ሰው ወይም ደግሞ ክስ የተመሰረተበት ሰው ከማንኛውም ሰው ጋር የመገናኘት፣ በትዳር አጋር፣ በቅርብ ዘመዶች፣ በጓደኞች፣ በሀኪም፣ በኃይማኖት አባት እና በህግ አማካሪው የመጎብኘት መብት አለው፡፡“ ታዲያ ለምንድን ነው አንዳርጋቸው ህገመንግስታዊመብታቸውን በወያኔ የተከለከሉት?
አንዳርጋቸው ምንም ዓይነት ግንኙነት እና የህግ ሂደት ሳይኖር አሁን ባሉበት ሁኔታ እንዲቀጥሉ ይደረግ ይሆናል፡፡ እንደ ደኃ ከረጢት ተቆርጦ እና ተቆራርጦ የተለጣጠፈው እና የተደረተው የቪዲዮ ማስረጃ እንደሚያሳየው አንዳርጋቸው በአልታወቁ ጊዚያት ቢያንስ በአምስት የተለያዩ አጋጣሚዎች እንደተጠየቁ ያመላክታል፡፡ ሆኖም ግን የመለማመጃው የጀማሪዎች የቪዲዮ ቀረጻ እየተቆረጡ እና እየተቀጠሉ የተለጠፉ ቢሆንም የተበላሸውን የ10 ደቂቃ ከ31 ሰከንድ የቪዲዮ ቀረጻ ማስረጃ ለማዘጋጀት ምን ያህል ጊዜ እንደተጠየቁ ለማወቅ አይቻልም፡፡
ሁሉም የአንዳርጋቸው የቪዲዮ ቀረጻ ማስረጃዎች የተዘጋጁት በህገወጥ መልኩ ኃይልን በመጠቀም በማስገደድ መሆኑ ጥያቄ የሚቀርብበት ጉዳይ አይደለም፡፡ ያንን ያህል ብዛት ያላቸውን ጥያቄዎች በአንድ ጀንበር ብቻ ሊመልሱት አይችሉም፡፡ አንድ ተጠርጥሮ በፖሊስ ወይም ደግሞ በፍርድ ቤት ባሉ ባለስልጣናት በቁጥጥር ስር ያለ ተጠርጣሪ ወይም ተከላካይ የሚቀርብ ጥያቄ ምርመራ ነው፡፡ ማናቸውም መልሶች በተለይም ደግሞ እራስን በማውገዝ የሚሰጡ መልሶች በፍርድ ሂደቱ ላይ ያሉ ሰዎች ካሏቸው የስብዕና መልሶች በተለየ መልኩ ያለውድ በግድ ቅቡል የሆኑ ወይም ደግሞ እምነት የተሰጠባቸው ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ ህገመንግስት አንቀጽ 19 (5) የባለስልጣኖችን የግዳጅ የምርመራ ጥያቄ እንዲህ በማለት ይከለክላል፣ “ማንኛውም ሰው በህግ ስነስርዓት ሂደቱ ጊዜ በጥቅም ላይ ሊውሉ የሚችሉ በግዳጅ የእምነት ቃል ወይም ደግሞ መረጃ ሊሰጥ አይችልም፡፡“ የአንዳርጋቸው የቪዲዮ ቀረጻ የእምነት ማስረጃዎች በዝንጀሮው የይስሙላ ፍርድ ቤት የሸፍጥ የፍርድ ሂደት ላይ በጥቅም ላይ ሊውሉ የሚችሉ አይደሉምን?
የአቶ አንዳርጋቸው የቪዲዮ ቀረጻ ማስረጃ ምላሾች የተዘጋጁት እርሳቸው በእስር ቤት ውስጥ ባሉበት ሁኔታ፣ ከማንም ጋር እንዳይገናኙ ሆነው (ከቤተሰብ፣ ከጓደኛ፣ ከህግ አማካሪ ፍጹም እንዳይገናኙ ተደርጎ) እና የህግ ጠበቃ በሌለበት ሁኔታ ነው፡፡ ስለሆነም እርሳቸው የሰጧቸው መልሶች በእርግጠኝነት በግዳጅ የተሰጡ መሆናቸው አያጠራጥርም፡፡ ሁሉም ተጠርጣሪዎች በወያኔ የሽብር ወንጀል የሚል ክስ የሚመሰረትባቸው ስለሆነ የህግ የምክር አገልግሎት እንዲያገኙ እና ህገመንግስታዊ መብታቸውን እንዳይጠቀሙ በኃይል ስለሚከለከሉ የአንዳርጋቸው ጽጌም ምርመራ እና ተጨማሪ ማስረጃ ለማግኘት ሲባል የተፈጸመባቸው አካላዊ እና የስነ ልቦና ስቅይት በግዳጅ ህገወጥ ድርጊት ላይ የተመሰረተ መሆኑን ያመላክታል፡፡ (ቀደም ሲል “ልዩ የሆነ የወንጀል ተውኔት” በሚል ርዕስ ያቀረብኩትን ትችት ልብ ይሏል፡፡)
የአንዳርጋቸውን የቪዲዮ ቀረጻ ምስል ከተመለከትን በኋላ ምን ዓይነት የህሊና ዳኝነት እንድንሰጥ የተፈለገው? ለመሆኑ የመጨረሻው የህሊና ፍርድስአንዳርጋቸውን አንድንሰጥ የተፈለገው ከብረት ምሰሶ ጋር አስሮማቃጠል ነውን!?
10 ደቂቃ ከ31 ሰከንዶች በወሰዱ ጊዚያት ተቆርጠው በተቀጠሉ የአንዳርጋቸው የቪዲዮ ቀረጻ ምላሽ ማስረጃዎች ላይ ብይንመስጠት፣
በአንዳርጋቸው የተሰጡ በ10 ደቂቃ የቪዲዮ ቀረጻ የተቀጠሉ እና የተለጠፉ ምላሾችን ዓላማ ወይም ደግሞ ይህንን በቅጥፈት የተሞላ የመድረክ ላይ ተውኔት ለህዝብ ዕይታ ማቅረብ ምን ፋይዳ ሊያመጣ እንደሚችል ለማወቅ መሞከር ለእኔ አጠቃላይ የሆነ ግራ የሚያጋባ ነገር ነው፡፡ አንዳርጋቸው የጽናት ተምሳሌት የሆኑ የአረብ ብረት ሳይሆኑ በወያኔ የማሰቃያ ክፍል ውስጥ በሚቀርብ የምርመራ ጥያቄ በቀላሉ የሚቀልጡ እና በነው የሚጠፋ ጥንካሬ የሚጎድላቸው ቀላል ነገር ናቸው ለማለት ተፈልጎ ነውን? የማሰቃያ የእስር ቤት ክፍል ውስጥ እንዲሰቃዩ በማድረግ ከወያኔ ግርፋት እና ስቅይት እንዲያገግሙ እና ትምህርት ወስደው የወሮበላነት ወንድሞቻቸውን እንዲቀላቀሉ ለማድረግ ታስቦ ነውን? ግንቦት ሰባት የተባለው ድርጅት ደካማ የሆነ እና ጠንካራ ወይም ደግሞ ብቁ የሆነ አመራር የሌለው እንዲሁም በቀጣይነት የህዝብ ድጋፍ የማያገኝ አስመስሎ ለማቅረብ የተዘየደ የሞኞች ብልሀት ነውን? አንዳርጋቸው በትጥቅ ትግል በእርግጠኝነት እምነት እንደሌላቸው እና አስመሳይ እንደሆኑ በማስረገጥ ሆኖም ግን በሰላማዊ ትግል እንደሚያምኑ እና ለእርሳቸው እና ለድርጅታቸው እንዲሁም ለጓደኞቻቸው የዘንባባ ዝንጣፊ በመያዝ ለመስጠት ታስቦ ነውን? በእራሳቸው ድርጅት ወይም ጓደኞች ዘንድ እምነት የሌላቸው ለዓላማቸው በጽናት ያልቆሙ አስመስለው ለማቅረብ ቋምጠው ነውን? በሌሎች የተቃዋሚ ድርጅቶች አመራሮች እና ድርጅቶች እንዲሁም በግለሰቦች ላይ ንቀትን የሚያሳዩ ናቸው በማለት ለማሳየት ፈልገው ነውን? በተወሰኑ የወያኔ መሪዎች እና በእራሱ የወያኔ ድርጅት ላይ ጥልቅ የሆነ ጥላቻ ወይም ፍቅር አላቸው የሚለውን ለማሳየት ነውን? እርሳቸው መጥፎ እንደሆኑ፣ የሞራል ሰብዕና የሌላቸው እና ሊታመኑ የማይችሉ እምነተቢስ ሰው እንደሆኑ ለማሳየት ተፍልጎ ነውን? በታማኝነት እና እነርሱ በሚፈልጉት መንገድ ላቀረቧቸው ጥያቄዎች ሁሉ ትክክለኛውን መልስ ሰጥተዋል በሚል ምክንያት አንዳርጋቸው ምክንያታዊ ሰው ናቸው ለማለት ተፈልጎ ነውን?
ለወገኖቼ እና ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ድምጼን ከፍ አድርጌ መጮህ እንድችል የ10 ደቂቃ ከ31 ሰከንድ የቪዲዮ ቀረጻውንየገሀነምነት ዓላማ ሊነግረኝየሚችል ሰው ሊኖር ይችላልን!?!
የ10 ደቂቃ ከ31 ሰከንድ ያህል ቆይታ ያለው የቪዲዮ ቀረጻ ማስረጃ በአምስት የተለያዩ አጋጣሚዎች በመምረጥ ከተለያዩ የቪዲዮ ክፍሎች ተቆርጦ እና ተለጥፎ የተዘጋጀ በእውነታ ላይ ሳይሆን በቅጥፈት ድሪቶ ላይ ተመስርቶ የተደረተ የሸፍጠኞች የማስመሰያ እና የማታለያ ቅጥፈት ነው፡፡ ሆኖም ግን ግቡን መታ ሊባል የሚችለው የሚታለል ሞኝ ሲገኝ ብቻ ነው!
በሌላ በኩል ደግሞ ጥቂት የሆኑት የቪዲዮው ክፍሎች ተመርጠው ከአንድ ወይም ከሁለት በላይ ከሆኑ የተንዛዙ መጠይቆች በቆረጣው መቀሳቸው እየተቆረጡ ተለጥፈዋል፡፡ የቪዲዮ ቀረጻው የአርትኦ ስራ እና የቆረጣ እንዲሁም የመለጠፍ ስራዎች በጣም አስቀያሚ እና እጅ እግሩ የማይያዝ ዝብርቅርቁ የወጣ በአንዳርጋቸው ተሰጡ የተባሉት መልሶች የእርሳቸውን የፖለቲከ እምነት እና በተወሰኑ ጉዳዮች ላይ የሚሰጧቸውን ትንታኔዎች ብስለት ሊያስገነዝቡ ይቅር እና ሰዋስዋዊ ይዘታቸው እንኳ የማይጨበጥ እና የማይዳሰስ ምንም ዓይነት ትርጉም የማይሰጡ ሆነው የተስተዋሉ በመሆኑ ነገሩን የበለጠ እንዲወሳሰብ አድርጎታል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በርካታዎቹ የቪዲዮው ክፍሎች የቅጥፍና ስልቱን ለማሳለጥ እና የተዛባ ግንዛቤ ለመፍጠር በሚል እኩይ ምግባር በአንድ ላይ እንዲታጀሉ በማድረግ ማቋረጫ በሌለው መልኩ ቀረጻውን በማካሄድ አንዳርጋቸው በእርግጠኝነት ምን ዓይነት ስብዕና ያላቸው ሰው እንደሆኑ ለማስመሰል ተሞክሯል፡፡
ይህንን የቪዲዮ ቀረጻ አጠናቅቀው እንዲለቀቅ ያደረጉትን ሰዎች ለህዝብ የህሊና ፍርድ ዳኝነት ሲሉ ሙሉውን ጥያቄ ምንም ዓይነት ቆርጦ ቀጥል የቅጥፈት ስልት ሳይጨመርበት መልቀቅ እንዲችሉ እጠይቃቸዋለሁ፡፡
የአንዳርጋቸው የመጀመሪያው የቪዲዮ ቀረጻ ምላሾች 10 ደቂቃ ከ31 ሰከንዶች ከሚወስደው አጠቃላይ ጊዜ ውስጥ 20 ሰከንዶችን በመውሰድ ይጀምራል፡፡ በዚያ ክፍል ውስጥ ሁለት ጎንዮሽ እና በክንዶቻቸው ላይ ነጠላ የሆነ ነጭ ጠቃጠቆ ከአረንጓዴ የውስጥ ሸሚዝ ጋር በነጭ ዚፕ የተዘጋጀ የአትሌት ልብስ ለብሰዋል፡፡ መደቡ ነጭ በሆነ ወንበር ላይ የተቀመጡ ይመስላል፡፡ (መርማሪዎቹ ስለምርመራ አቀራረቡ ቀደም ሲል ካቀረብኩት ትንታኔየ ትምህርትን የቀሰሙ ይመስላል እናም በአንዳርጋቸው የምርመራ ጉዳይ ላይ የምርመራው ቦታ የት እንደሆነ እና በምን ጊዜ እንደተደረገ የሚያሳይ ምንም ዓይነት ፍንጭ አያመላክትም፡፡ ሁሉንም ነገር በድብቅና በስውር ለመፈጸም ጥረት ባደረጉ ቁጥር በእርግጠኝነት ሁሉንም ነገር ይፋ እንደሚያወጡት ሊያውቁት ይገባል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ወረድ ሲል የምመጣበት ይሆናል፡፡) ከአንዳርጋቸው በስተቀኝ በኩል በምርመራ ጠረጴዛው ላይ ያልተከፈተ በፕላስቲክ ውስጥ ያለ ውኃ ይታያል፡፡ ይኸኛው የቪዲዮ ቀረጻ ክፍል በ30፣ 41 እና 55 ሰከንዶች… በድምሩ በ2 ደቂቃ ከ6 ሰከንዶች ተከፋፍሎ የቀረበ ነው፡፡ የመጀመሪያውን ወጥ የሆነውን የቪዲዮ ቀረጻ እንደ ስጋ እየመተሩ በአስከፊ ሁኔታ በጣጥሰውታል፡፡ እናም ማንም የአንዳርጋቸውን መልስ ለመገንዘብ የሚፈልግ ሰው ሁሉ ዲጂታል በሆነ መልኩ የተገጣጠሙትን የአንዳርጋቸውን ምስሎች በአንክሮ በማየት እና በቪዲዮ የምርመራ ስልት አፋቸውን ሲያንቀሳቅሱ በመመልከት አገጣጥሞ ለመተርጎም እና በመጠኑም ቢሆን ምን ለማለት እንደፈለጉ ግንዛቤ ለመውሰድ ይቻላል፡፡
ሁለተኛው የቪዲዮ ቀረጻ ክፍል በ4 ደቂቃ ከ29 ሰከንድ ላይ ይጀምራል፡፡ አንዳርጋቸው ቀደም ሲል በመጀመሪያው የቪዲዮ ቀረጻ ክፍል የምርመራ ወቅት ለብሰውት የነበረውን ጃኬት እና በአንገቱ ዙሪያ ነጭ ቀለም ያለው ፈጋ ያለ ውኃ ሰማያዊ ቀለም ያለው ሸሚዝ ለብሰዋል፡፡ ከአንዳርጋቸው በስተቀኝ በኩል ከምርመራ ጠረጴዛው ላይ በከፊል የሚታይ የኤሌክትሮኒክ መሳሪያ ይታያል፡፡ ይኸኛው የቪዲዮ ቀረጻ ክፍልም እንደዚሁ የተቆራረጠ እና በአስከፊ ሁኔታ ለበርካታ ጊዚያት እንደ ጥሬ ስጋ የተመተረ መሆኑን በግልጽ ያመላክታል፡፡
ሶስተኛው የቪዲዮ ቀረጻ ክፍል ደግሞ በ5 ደቂቃ ከ20 ሰከንዶች ላይ ይጀምራል፡፡ በዚህኛው የቀርጥራጭ ክፍል አንዳርጋቸው በእጅጌው ላይ ነጭ ቀለም ያሰነበረበት ጥቁር አዲዳስ የአትሌት ቱታ ለብሰዋል፡፡ የቪዲዮ ቀረጻው መደቡ ነጭ በሆነ በአንድ ጊዜ የቀረጻ ተኩስ የተወሰደ መሆኑን ይመሰክራል፡፡ የምርመራ ጠረጴዛው ሙሉ በሙሉ በትክክል አይታይም፡፡ እንደዚሁም ደግሞ የቪዲዮ ቀረጻው በረዥም ጊዜ የምርመራ ጥያቄ በመታጀብ ለበርካታ ጊዚያት ተቆርጦ የተቀጠለ ድሪቶ መሆኑን በግልጽ ያመላክታል፡፡
አራተኛው የቪዲዮ ቀረጻ ክፍል በ8 ደቂቃ ከ33 ሰከንድ ላይ ይጀምራል፡፡ አንዳርጋቸው በቪዲዮ ቀረጻው ክፍል 1 እና 2 የለበሱትን ዓይነት ሰማያዊ ጃኬት ለብሰዋል፡፡ ሶስተኛው የቪዲዮ ቀረጻ ክፍል የክፍል 1 እና 2 ቀጣይ መሆኑን የሚያመላክት ግልጽ የሆነ ነገር የሌለ ሲሆን አንዳርጋቸው የሚሰጧቸውን ምላሾች ለመድረክ ትወና አጋንኖ ለማቅረብ ሲባል ቆርጦ የመቀጠሉ ተግባራት በሰፊው ተሰርቷል፡፡ በዚህ ክፍል የቪዲዮ አርታዒዎቹ እና የቪዲዮ ቀረጻ ስራውን የሚያዘጋጁት ሰዎች ምን ለመስራት ና አንዳሰቡ ማወቅ አይቻልም፡፡ (አንደዚህ አይነት አሳፋሪ ስራ ከመስራት በፕሮፓጋንዳ ፊልም ወይም በሌላ ተመሳሳይ ስራ ላይ ስልጠና ቢወስዱ ከትዝብትና መሳቅያ ከመሆን ያድናቸዋል፡፡)
አምስተኛው የቪዲዮ ፊልም ቀረጻ ክፍል በ9 ደቂቃ ከ36 ሰከንድ ላይ ይጀምራል፡፡ አንዳርጋቸው በቪዲዮ ቀረጻው ክፍል 1 እና 2 የለበሱትን ዓይነት ሰማያዊ ጃኬት ለብሰዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ አስስተኛው የቪዲዮ ቀረጻ ክፍል በተለያዩ ነጥቦች ላይ ረዥም የሆነ የመቁረጥ እና የመቀጠል ስራዎች ተከናውነውበታል፡፡
እንደቅርጫ ስጋ እና እንደጥሬ ስጋ በተከፋፈለ እና በተመተረ የሸፍጥ መረጃ ላይ መሰረት በማድረግ እንዲሁም የት እና መቸእንዲሁም ማንነታቸውባልታወቁ የቪዲዮ ቀረጻ ቆርጦ ቀጥሎች በተዘጋጀው የመድረክ ትወና ዝግጅት ላይ ህብረተሰቡ የህሊናፍርድ እንዲሰጥ ተጋብዟል፡፡ የአንዳርጋቸው ምላሾች ጥያቄ አልባዎች ናቸው፡፡ ምላሾቹ በርካታ የሸፍጥ የአርትኦ ስራ ተሰርቶባቸዋል፣ የተወሰኑ የቪዲዮ ቀረጻ ክፍሎችን ብቻ መሰረት በማድረግ በአንዳርጋቸው ላይ ለተመልካች መጥፎ ስዕል እንዲሰጥ በማሰብ በመርማሪዎች እምነት ስራው ግቡን መታ ለማለት እንዲቻል ተቆርጠው እንደገና ከእነርሱ ጋር በማይሄዱ እና በማይስማሙ የቅጥፈት ቁርጥራጮች በአንድነት ተቀጥለዋል፡፡ በአምስቱም የቪዲዮ ቀረጻ ክፍሎች ላይ አንዳርጋቸው ይቅርታ ጠያቂ፣ ጸጸት የተሰማቸው ለማስመሰል፣ እርግጠኛ ያልሆኑ፣ ከጠለፋው በፊት የነበረውን የእራሳቸውን ህይወት የሚያወግዙ፣ በዓላማ ጓደኞቻቸው እና በድርጅታቸው ላይ ጣቶቻቸውን የሚቀስሩ፣ ብልህነት የጎደላቸው፣ የሚያደናግሩ፣ ኃይል የተቀላቀለባቸው፣ ጸጸት እንዲደረግ የሚገፋፉ፣ አሳፋሪ ስብዕናን የተላበሱ፣ የጥፋትኝነት ስሜትን የተከናነቡ፣ አሳዛኝ፣ አዋራጅ፣ ህሊናን የሚያስቱ፣ በቅሌት የሚዘፍቁ፣ እርባናየለሽ የሆኑ፣ ማጭበርበር የተሞላባቸው፣ ወዘተ ምላሾች እንዲሰጡ ጥንቃቄ በተመላበት መልኩ ወያኔ ጥረት አሳይቷል፡፡ እንግዲህ በዚህ ዓይነት ሁኔታ በተቀረጸ የቪዲዮ የቅጥፈት የምላሽ ማስረጃ ነው የወያኔ ዓይን አውጣ የወሮበላ ስብስብ ተመልካች የሆነውን የኢትየጵያ ህዝብ እና የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ በአንዳርጋቸው ላይ የህሊና ፍርዳቸውን እንዲሰጡ እየጠየቀ ያለው፡፡
ያም ሆነ ይህ በአንዳርጋቸው ላይ የህሊና ፍርድ እንድንሰጥ የቀረበልንን ግብዣ እቀበላለሁ!
የአንዳርጋቸው ጽጌ የፍርድ ሂደት በእኔ የህሊና ዳኝነት፣
በቪዲዮ ቀረጻው በቀረቡት 10 ደቂቃ ከ31 ሰከንዶች ቆይታ በነበራቸው የወያኔ የቪዲዮ ቀረጻ ወካይ የሚሆኑ ምላሾች ላይ መሰረት በማድረግ በአንዳርጋቸው ጽጌ ተሰጡ በተባሉት ምላሾች ላይ ያለኝን የህሊና ዳኝነት እነሆ፡፡ ከዚህ በታች የቀረቡትን የእኔን ፍርድ አንባቢዎቼ ካነበባችሁ በኋላ የሰጠሁት ፍርድ የዝንጀሮ የይስሙላ ፍርድ ነው ልትሉኝ እንደምትችሉ ጥርጥር የለኝም፡፡ ሆኖም አንድታቁለኝ የምፈለገው እኔ ቢያንስ አውነተኛና ፍትሀዊ የሆንኩ የዝንጀሮ የይስሙላ ፍርድ ቤት ነኝ፡፡
የቪዲዮ ቀረጻውን በተመለከተ በአንዳርጋቸው የምርመራ ጥያቄ ላይ የእኔን የህሊና ፍርድ መግለጫዎች እና ማብራሪያዎች ከዚህ እንደሚከተለው አቀርባለሁ፡፡ በአንዳርጋቸው ላይ የቀረበው የቪዲዮ ምስል የዕይታ ጥራቱ በጣም ደካማ የሆነ፣ ምንም ዓይነት እውቀት በሌላቸው ተለማማጅ የቪዲዮ ኦዲዮ ቀራጮች ተቆርጦ፣ ተቀጥሎ፣ ተጥፎ እና ተደርቶ የተዘጋጀ መሆኑን መሰረት በማድረግ የህሊና ፍርዴን እሰጣለሁ፡፡ አንዳርጋቸው ለየትኞቹ ጥያቄዎች ምላሽ እየሰጡ እንደሆነ በምንም ዓይነት መልኩ ባወጣ ባወርደው ልገነዘበው አልቻልኩም፣ ልገነዘበው ያልቻልኩት ደግሞ የመገንዘብ ችግር ወይም የቋንቋ እጥረት ኖሮብኝ ሳይሆን የቀረበው የልጆች ተረት ተረት ጨዋታ፣ ምንም ዓይነት ግንዛቤን ሊፈጥር የማይችል በቅጥፈት የተሞላ የሸፍጠኞች ድሪቶ እዚህም እዚያም የሚረግጥ አራምባ እና ቆቦ ሆኖ በመገኘቱ ብቻ ነው፡፡ አቶ አንዳርጋቸው የሰጧቸው ምላሾች በቪዲዮ ተቀርጸው እና በቆርጦ ቀጥል የወያኔ ስልት ተጥፈው፣ ተለብደው እና ተሸሞንሙነው ለህዝብ የህሊና ዳኝነት የቀረቡ ከመሆናቸው ውጭ በእርግጥ የሀሰት ውንጀላ ሰለባው ጉዳዩን አውቀው በእራሳቸው አንደበት አምነውበት በተጽዕኖ አንደሰጡ ምንም ጥረጣሬ የለኝም፡፡ እንደዚሁም ደግሞ እነዚህ በቪዲዮ ተቀርጸው ከተጠናቀቁ በኋላ በወያኔ የመቁረጫ መቀስ ተቆርጠው፣ በወያኔ መርፌ ተሰፍተው፣ ተደርተው እና ተለብደው የቀረቡ ለመሆናቸው አንዳርጋቸውን ጥፋተኛ አድርጎ በህዝብ ህሊና ውስጥ የተዛባ አመለካከት ለመፍጠር እና እርሳቸውን ከማጥ ውስጥ ለመጨመር የተፈበረከ የመድረክ ላይ ውኔት መሆኑን አውቃለሁ፡፡ አንዳርጋቸው ቀደም ሲል ተሰጥተዋቸው የነበሩትን በጥያቄ አቅራቢዎቻቸው ለሚሰጡ ጥያቄዎች ተደጋጋሚ ምላሽ እየሰጡ እና እየደገሟቸው መሆኑን አውቃለሁ፡፡
የአንዳርጋቸው አዕምሯዊ እና አካላዊ ደህንነት አስተማማኝ በሆነ መልኩ ሙሉ ጤንነትን የተላበሰ መሆኑን ባላወቅሁበት ሁኔታ እና ምንም ዓይነት መረጃ ወይም ፍንጭ ባላገኘሁበት ሁኔታ ላይ ነው ይህንን የመሰለ የህሊና ዳኝነት አስተያየት በመስጠት ላይ ያለሁት፡፡ አቶ አንዳርጋቸው በግዳጅ ምላሽ እንዲሰጡ ከመደረጋቸው በፊት በጠያቂዎቻቸው አማካይነት አደንዛዥ እና አዕምሮን የሚያስት መድኃኒት ተሰጥቷቸው ይሁን አይሁን ወይም ደግሞ አዕምሯቸውን ሊለውጥ የሚችል ሌላ የማሰናከያ ወጥመድ ተጠምዶላቸው ይሁን አይሁን በእርግጠኝነት የማውቀው ነገር የለም፡፡ አንዳርጋቸው አካላዊ እና ስነልቦናዊ ጫና እና ማሰቃየት ወይም ደግሞ ምላሾችን እንዲሰጡ ኃይል የተቀላቀለበት ማስገደጃ የተደረገባቸው ለመሆናቸው እውቀቱ ሳይኖረኝ (ሆኖም ግን ከፍተኛ የሆነ ጥርጣሬ አለኝ) ነው ይህንን የህሊና ፍርድ በመስጠት ላይ ያለሁት፡፡ አንዳርጋቸው ምላሾችን እንዲሰጡ ከመገደዳቸው በፊት ለበርካታ ጊዚያት እንቅልፍ ተከልክለው እንደሆነ ወይም ደግሞ ምግብ ወይም ሁለቱንም እንዳያገኙ ተደርገው እንደሆነ የማውቀው ምንም ዓይነት ፍንጭ የለኝም፡፡ (በመጀመሪያው የቪዲዮ ቀረጻ ክፍል ውስጥ ያልተከፈተ የፕላስቲክ ውኃ በጠረጴዛው ላይ ተቀምጦ ይታያል፡፡ ይህ ውኃ አንዳርጋቸው ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች በሙሉ ለወያኔው አጥጋቢ የሆነ ምላሽ መስጠት ከቻሉ ከጥያቄ እና መልስ ሂደቱ መጠናቀቅ በኋላ በሽልማት መልክ ሊሰጡ የታቀደ ነውን? ነው ወይስ ደግሞ መድረኩን ለማስዋብ ተብሎ የተቀመጠ ነው? አንዳርጋቸው በቪዲዮ ቀረጻ ምስሎች ላይ ደማቅ ጠቆር ያለ የአትሌት ልብሶችን ለብሰው ከመታየታቸውም በላይ ፊታቸው ብቻ ተነጥሎ እንዲታይ ተደርገዋል፡፡ ይኸ ሁኔታ በዚህ ዓይነት አለባበስ እንዲታዩ መደረጉ ምናልባትም በሰውነታቸው ላይ ጉዳቶችና የማሰቃየት ውጤት የሆኑት ጠባሳዎች እንዳይታዩ ከህዝብ ዕይታ ለመደበቅ ተብሎ በሸፍጥ መሰሪዎቹ የተቀነባበረ ድርጊት ሊሆን ይችል ይሆን?
እኔ አሁን በዚህ መድረክ በአንዳርጋቸው ጉዳይ ላይ የህሊና ፍርዴን እና አስተያየቴን በመስጠት ላይ ያለሁት መሰጠት ያለባቸው ምላሾቹ አስቀድመው በተዘጋጁበት፣ ጥያቄዎቹ ምን እንደሚሉ እና ማንስ እንደሚጠይቅ ባልታወቀበት፣ በአጠቃላይ የተሟላ መረጃ በሌለበት እና አስቀድሞ እቁቡ በተበላበት የቅጥፈት የትወና መድረክ ላይ ሆኘ ነው፡፡ አንዳርጋቸው በሙሉ ቃለ መጠይቁ ወቅት ለጠያቂዎቻቸው ምን እንዳሉ እና ምንስ እንዳላሉ ምንም ዓይነት እውቀት ሳይኖረኝ ነው በቀጥታ ወደ ማጠቃለያ መደምደሚያው እመር በማለት የእኔን የህሊና ፍርድ እና አስተያየት በመስጠት ላይ ያለሁት፡፡ አቶ አንዳርጋቸው ይህ ጥያቄ የቀረበላቸው በየት ቦታ እና በምንስ ጊዜ እንደሆነ ምንም ዓይነት መረጃ ሳይኖረኝ፣ የጠያቂዎቻቸው ማንነት ባልታወቀበት ሁኔታ፣ ሲቀርቡላቸው የነበሩት ጥያቄዎች ብዛት እና ዓይነት ምን እንደሆነ ባልታወቀበት፣ የሚሰጡት ምላሾች ለተወሰኑ ግልጽ ለሆኑ ጥያቄዎች መሆን አለመሆናቸው እና ይህንን የጥያቄ እና መልስ ሂደት እንዲከናወን ትዕዛዝ የሰጡት ባለስልጣኖች ማንነት እና ከዚህ ቃለ መጠይቅ በኋላ የተገኘውን ምላሽ ለህዝብ በመልቀቅ የህሊና ዳኝነት እንዲሰጥ በመጠየቅ ላይ ያለው እና ከዚህ በመነሳት ምን ዓላማን ለማራመድ እንደሆነ በግልጽ ብቻም ሳይሆን በግርድፉም ቢሆን ባልታወቀበት ሁኔታ ነው ይህንን የህሊና ዳኝነት እና አስተያየት በመስጠት ላይ ያለሁት፡፡ አንዳርጋቸው ለአንድ ወይም ከአንድ በላይ ለሆኑ ጥያቄ አቅራቢዎች ምላሽ የሰጡ መሆን አለመሆናቸውን ባላወቅሁበት ሁኔታ ላይ ነው ይህንን የህሊና ፍርድ እና አስተያየት በመስጠት ላይ ያለሁት፡፡ በበርካታዎቹ የቪዲዮ ቀረጻ ክፍሎች ውስጥ የአቶ አንዳርጋቸው ዓይኖች ምላሽ በሚሰጡበት ክፍል ውስጥ በፍጥነት ከማዕዘን ወደ ማዕዘን ከግድግዳ ወደ ግድግዳ ሲንቀዋለሉ እና ሲያማትሩ የመስተዋላቸው ሁኔታ በጥያቄ እና መልስ የመስጠት ሂደቱ ወቅት በርካታ ጠያቂዎች የነበሩ ለመሆኑ ማስረጃ ሊሆን ይችላል፡፡ አንዳርጋቸው በተናገሯቸው እና በቀረቡት ቁርጥራጭ መረጃዎች ላይ መሰረት በማድረግ ነው እንግዲህ የእኔን የህሊና የዳኝነት እና አስተያየት በመስጠት ላይ ያለሁት፡፡
ስለሆነም በአንዳርጋቸው ጥያቄ አልባ በሆኑ በዚህች ምድር ላይ ለወሮበሎች በተሰጡ ምላሾች ላይ የእራሴን ፍርድእሰጣለሁ፡፡
የአንዳርጋቸው አስረጅነት፡ “ባለፈው ጊዜ የብሩህ አዕምሮ ባለቤት የሆኑት ተማሪዎች ነበር ወደ ፖለቲካው ዓለም ይገቡ የነበሩት፡፡ በሂደት በሞት የተለዩትን (በፖለቲካ የትግል ሂደት ውስጥ) የእነዚህን ተማሪዎች ስም ዝርዝር ባቀርብ እጅግ በጣም ትደነግጣላችሁ፡፡”
ይኸ ትክክለኛ መግለጫ ነው፡፡ በርካታዎቹ የባለብሩህ አዕምሮ ባለቤቶች፣ የመጠቀ ሀሳብ አፍላቂዎች እና አራማጆች፣ እንዲሁም ጀግኖች እና ጀግኒቶች ወጣቶች እ.ኤ.አ በ1970ዎቹ በአምባገነኑ ወታደራዊ አገዛዝ እንዲያልቁ ተደርጓል፡፡ ሌሎች ድርጅቶች ወጣቱን ትውልድ የእራሳቸውን የፖለቲካ ዓላማ ለማራመድ እንደ ዝቅተኛ ማዕረግ እንዳላቸው ወታደሮች በማድረግ ተጠቅመውባቸዋል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ጥቂቶችን አውቃለሁ፡፡ አንድ ቀን ታሪካ እነዚህን ወጣቶች ከእነርሱ ትውልዶች ምርጦች እና የባለብሩህ አዕምሮ ባለቤቶች በማለት ሊያስታውሳቸው ይችላል፡፡
“አንዳርጋቸው፡ በአሁኑ ጊዜ ያሉ ወጣቶች ዲግሪዎቻቸውን ካገኙ እና ለትንሽ እድል ከበቁ ወደ ውጭ ሀገር ሄደው ነው የሚኖሩት፡፡ እዚያም ከሄዱ በኋላ ስራ ያገኛሉ እናም ኑሯቸውን እዚያው ይቀጥላሉ፡፡ እነዚህ ወጣቶች እንዲያውም በሀገራቸው ውስጥ ለመቆየት እና ለመኖር የሚችሉ አይመስላቸውም፡፡ በዚያ ዓይነት መልኩ አያስቡም…”
ይሄማ የማይካድ እውነታ ነው፡፡ እስቲ እውነተኞች እንሁን፡፡ ማንም ወንድም ሆነ ሴት ወጣት ያለመውን ህልም እውን ለማድረግ እንዲችል ነጻነቱን የሚያጎናጽፍ ሀገር ሲያገኝ ከኢትዮጵያ ወደዚያ ወደ ውጭ ሀገር የማይሄድ ወጣት ማን አለ? ምንም ከማያውቁ የደናቁርት ስብስቦች እና በሙስና እስከ አንገታቸው ድረስ ከተዘፈቁ ወሮበላዎች ጋር እዚህ ኢትዮጵያ ውስጥ መኖርን የሚመርጥ ወጣት ሊኖር ይችላልን?
አንዳርጋቸው፡ “ግንቦት 7 በብዙ መንገዶች በወጣቶች ላይ የሚያተኩር ድርጀት ነው፡፡ ወጣቶች በሰላማዊ ትግል ላይ እምነት አላቸው፣ እናም እንደ ዱሮው የኢህአፓ ወጣት ሁሉ መሞትን አይፈልጉም፡፡ ያ ያለፈበት ጊዜ ነው… ወጣቶች እንዲህ ይላሉ፣ “እራሳችንን መግለጽ እንችላለን፣ በግልጽ በአደባባይ ወጥተን ተቃውሟችንን ማሰማት እንችላለን፡፡ በእኛ ላይ የሚደርስብን አንዳችም ነገር የለ፡፡ የአሁኑ ዘመን ሌላ ጊዜ ነውና””
በዚህ በክፍል 1 የቪዲዮ ቀረጻው ክፍል ላይ የቀረበው ምላሽ አስከፊ በሆነ መልኩ ተቆርጦ ተቀጥሏል፣ እንዲለጠፍም ተደርጓል፡፡ ስለሆነም አንዳርጋቸው የትኛውን ክፍል ለመጥቀስ እንደፈለጉ ለማወቅ በጣም አስቸጋሪ ነው፡፡ ምላሻቸውን በትክክል ተገንዝቤው ከሆነ እውነት ነው የኢትዮጵያ ወጣቶች ሰላማዊ የሽግግር ለውጥን ይፈልጋሉ፡፡ ለውጥን ከፍቅር እና እውቀት ጋን ውስጥ እንጅ ከድንቁርና እና ከAK-47 የጠብመንጃ አፈሙዝ ፈጽሞ አይፈልጉም፡፡ አንድም ኢትየጵያዊ የሆነ ወጣት በእውቀት እና በጉብዝና ላይ በተመሰረተ መልኩ ከሰላም ይልቅ ጦርነትን፣ ከፍቅር ይልቅ ጥላቻን እና ከወንድማዊነት ጠላትነትን ይመርጣል የሚል የማውቀው አንድም ወጣት የለም፡፡
አንዳርጋቸው፡ “ግንቦት 7 አሳሳቢ የሆኑ ችግሮች አሉበት፡፡ ከዚህ ቀደም ያላየናቸው እና ወደፊት ግን ማየት ያለብን ነገሮች እንዳሉ እንገደዳለን…ዋና ዋና ተግባራት ናቸው ያልናቸውን ተግባራት እስካሁን ድረስ አላከናወንንም…“
ለእኔ ይህ መግለጫ ታማዕኒነት ያለው ይመስለኛል፡፡ ስግንቦት 7 ውሰጣዊ አሰራር እና ሂደት የማውቀው ነገር የለኝም፣ ሆኖም ግን ከአንዳርጋቸው ምላሽ ለመገንዘብ እንደቻልኩት በግንቦት 7 ላይ ያለው ችግር በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ባሉ በሌሎች በእያንዳንዱ የተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅት ላይም የሚንጸባረቅ ይመስላል፡፡ ምን ዓይነት አሰልች ድግግሞሽ ነው!
አንዳርጋቸው፡ “የኢትዮጵያ የተቃዋሚ የፖለቲካ ቡድኖች በፖለቲካ ሂደቱ ላይ እንዴት መንቀሳቀስ እና መስራት እንዳለባቸው ጥያቄ አለኝ፡፡ የተቃዋሚ የፖለቲካ ቡድኖች መንግስት ምን እየሰራ እንዳለ ግልጽነት በተመላበት ሁኔታ የማያውቁ ከሆነ ለመስራት እንዴት ዝግጁ እንደሚሆኑ ወይም ደግሞ የፕሮግራም ሰነዳቸውን/manifesto ወይም ደግሞ የምርጫ ዕቅዶቻቸውን እንዴት እንደሚያዘጋጁ እና እንደሚተገብሩ የማውቀው ነገር የለም፡፡ ግልጽነትን በተመለከተ ኃላፊነቱ ያለው በመንግስት ላይ ነው፡፡ ይህ የእኔ እምነት ነው፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ የተቃዋሚ ፖለቲካ ድኖች የተሰባበሩ ናቸው፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ይህንን ትልቅ ኃላፊነት ለመቀበል እና አንድ ሆነው በመተባበር ለመስራት ወደ አንድነት መምጣት አለባቸው… በጣም ግለሰባዊ የሆኑ የተወሰኑ እሴቶች አሉ…ለተቃዋሚ የፖለቲካ ቡድኖች አንዱ እና ዋናው ችግር ወደ አንድነት የመምጣት እና በሚያስማሟቸው ጉዳዮች ላይ የጋራ አጀንዳ ቀርጸው ለጋራ ዓላማ መንቀሳቀስ አለመቻላቸው ነው…የኢኮኖሚ ፖሊሲ ሲነድፉ እና ሲያወጡ አይቸ አላውቅም፡፡ የኢኮኖሚ ፖሊሲያቸው ምንድን ነው?…አንድ ሺህ የሚሆኑ ሰዎች በአንድ ላይ ተሰባስበው የፖለቲካ ፓርቲ ማቋቋም ይችላሉ… ወይም ደግሞ 5 ሰዎች የፖለቲካ ፓርቲ መስርተው ለስልጣን መወዳደር ይችላሉ በሚለው ሀሳብ ላይ እምነት የለኝም…ጥቂት የተቃዋሚ የፖለቲካ ቡድኖች ስብሰባ በሚያካሂዱበት ጊዜ፣ 20 ሰዎች ሊኖሯቸው ይችላል፣ ለምሳሌም የኢህአፓ፣ ሸንጎ፣ ወዘተ…የእኛ ሰዎች ሲጨመሩበት ደግሞ 23 ወይም ደግሞ 24 ሊሆን ይችላል…ምንም ዓይነት የዓላማ አንድነት ሳይኖራቸው እንደ ጥቅምት አክርማ ይሰነጠቃሉ፣ ይሰነጣጠቃሉ…“
ይህ በቪዲዮ ቀረጻ ክፍል 3 በተሰጠው ምላሽ ላይ አስከፊ በሆነ መልኩ ቆርጦ የተቀጠለ እና አንዳርጋቸው ስለተቃዋሚ የፖለቲካ ባህሪያት በትክክል ምን ለማለት እንደፈለጉ ለመገንዘብ በጣም አስቸጋሪ ነው፡፡ ሆኖም ግን የኢትዮጵያ የተቃዋሚ የፖለቲካ ቡድኖች የተሰባበሩ፣ የተበጣጠሱ፣ ወደ አንድነት ለመምጣት ያልቻሉ እና ህብረት ፈጥረው የህወሀትን ገዥ ፓርቲ ግንባር ለግንባር ለመጋፈጥ ያልቻሉ ናቸው የሚለው ሀሳብ የማይካድ ሀቅ ነው፡፡ የኢትዮጵያ የተቃዋሚ ፖለቲካ ቡድኖች የሀገሪቱን ችግሮች ለማስወገድ የሚያስችሉ የእራሳቸው ግልጽ እና በሚገባ የተቀመሩ ፕሮግራሞች ወይም ደግሞ የፓርቲ የፕሮግራም ሰነዶች/manifestos የሌሏቸው ናቸው፡፡ ከአምስት ዓመታት ገደማ በፊት የአውቀት መርሀግብር/think tank program በማዘጋጀት የተቃዋሚ የፖለቲካ ቡድኖች የተባበረ የፖለቲካ ሀሳቦች/agenda እና መርሀ ግብሮች እንዲኖሯቸው ሀሳብ አቅርቤ ነበር፡፡ (“እውነታውን ለእውነት ፈላጊዎች መናገር” በሚል ርዕስ አቅርቤው የነበረውን የሁፍንግቶን ፖስት ትች ቴን ይመለከቷል፡፡) እኔ በዚህ መልክ ካቀረብኩት ሀሳብ ላይ አንድም የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲ ወስዶ በስራ ላይ ለማዋል የሞከረ የለም፡!
በቪዲዮ ምስሉ ላይ የአንዳርጋቸው የመጨረሻ ምላሽ፡ አድናቆትን ልሰጣቸው (ስለ እኔ እስራት) የምችልባቸው በርካታ ነገሮች አሉ፡፡ ወደዚህ በመጣሁበት ጊዜ የለበስኳት ሸሚዝ እና ፓንት ብቻ ነው የነበረኝ፡፡ ከምግብ አንጻር ስኳርነት ከሌላቸው ምግቦች ውጭ እኔ እራሴ የመረጥኩትን የእኔ አሳሪዎች ሲታዘዙ የሚያቅርቡልኝን እጠቀማለሁ፡፡ እዚህ ከመጣሁ በኋላ በጣም ጤናማ ሆኛለሁ፡፡ ፍጹም በሆነ መልኩ በሚስማማ ሁኔታ ላይ እገኛለሁ፣ በምንም ዓይነት ሁኔታ የማይስማማ ነገር አላየሁም፡፡ በግቢው ውስጥ እራመዳለሁ፣ እንሸራሸራለሁ፣ እናም ሁሉንም የስባትነት የውፍረት ሁኔታዎችን ሁሉ አስወግጀ ሙሉ በሙሉ ሸንቃጣ እና ያማረበት ሰው ሆኛለሁ፡፡
በቡርጅ አል መለስ ዜናዊ ሆቴል ለሚደረገው የምግብ አሰራር አስተያየት ለመስጠት አልችልም፡፡ ሆኖም ግን በመለስ ዜናዊ የማጎሪያ እስር ቤት ውስጥ ለአንዳርጋቸው ጤንነት ተብሎ ከፍተኛ የሆነ ክብካቤ ይኖራል ብሎ ለማመን ጉምን በእጀ በመዳፉ እንደመዝግን የምቆጥረው ስለሆነ ጥርጣሬየ የበረታ ነው፡፡ እንደዚሁም ደግሞ አንዳርጋቸው እስከ አሁን ድረስ ከታዩት አሸባሪዎች ሁሉ በጣም “አደገኛ አሸባሪ” እንደሆኑ ተደርገው በወያኔ የወሮበላ ስብስብ ተነግሮናል፡፡ ለዚህም ነው እ.ኤ.አ በ2009 እና እንደዚሁም በ2012 ሁለት ጊዜ የሞት ፍርድ የተፈረደባቸው፡፡ በእርግጥም ወያኔ በጣም ረዥም ጊዜ ወስዶ ልዩ የሆነ የመድረክ ላይ ተውኔት አዘጋጅቶ ለህዝብ እይታ እና ለህሊና ዳኝነት በሚል አሳፋሪ ዘለፋ ለኢትዮጵያ ህዝብ ማቅረቡ አንዳርጋቸው አደገኛ ሰው ቢሆኑበት መሆኑ አጠራጣሪ አይደለም፡፡ እ.ኤ.አ ጁላይ 2014 አንዳርጋቸው የመን ላይ በወያኔው መጠለፋቸውን ተከትሎ ወያኔ አንዳርጋቸውን ከኦሳማ ቢንላደን ጋር መሳ ለመሳ በሆነ ቋንቋ አቅርቧቸው ነበር።
ለምንድን ነው የወያኔ ወሮበላ ስብስብ የኢትዮጵያ ኦሳማ ቢንላደን ናቸው እያለ ለሚያሰቃያቸው አንዳርጋቸው ጽጌ እንደዚህ ያለየንጉሳዊ ክብካቤ እያደረገሙሽራ አስመስሎ የያዛቸው???
ወያኔ አንዳርጋቸውን እንደዚህ ባለ የንጉሳዊ ቤተሰብ ክብካቤ ዓይነት አያያዝ እያቀማጠላቸው ከሆነ ለምንድን ነው 10 ደቂቃ ከ31ሰከንዶች በወሰደውምላሻቸው አንድ ጊዜ እንኳ ቢሆን የድሎት ፈገግታ ሳያሳዩ የመድረክ ትወናው የተጠናቀቀው? ለማያውቁሽ ታጠኝ! ነው ነገሩ፡፡
የአንዳርጋቸውን የቪዲዮ ቀረጻ ፊልም ቀደም ሲል ተመልክቸዋለሁ፣
የወያኔ የወሮበላ ስብስብ ብዙ ዓይነት ድንቁርናዎችን፣ ሰይጣናዊ እና ከአፍንጫ የማያልፉ አስተሳሰቦችን፣ ውስብስብ የሆኑ የማታለል ድርጊቶችን፣ የሞኝ እና የጅላጅል እኩይ ምግባሮችን ለበርካታ ዓመታት ሲፈጽም ቆይቷል፡፡ የወያኔ የወሮበላ ስብስብ የሸፍጥ ቪዲዮ አስቀርጾ እና አቀነባብሮ ሰላማዊ የሆኑ የሙስሊም ማህበረሰብ ተወካዮችን በሀገሪቱ ቴሌቪዥን በማሳየት አሸባሪ ናቸው በማለት የስም ማጥፋት ዘመቻውን ሲያጧጡፍ በታላቅ አግራሞት ስመለከተው ነበር፡፡ በሁለት አሳዛኝ እና በለማጅ የቪዲዮ ቀራጮች የተዘጋጁ የቪዲዮ ዘገባዎች ወያኔ የሙስሊሙ ህብረተሰብ ዋና ጽንፈኞች ናቸው በማለት ስም የማጥፋት ሙከራውን ሲያካሂድ ተስተውሏል፡፡ ወያኔው በሁለት የቪዲዮ ዘገባዎች ማለትም የደም መሬት/አኬልዳማ ወይም ደግሞ የሙስና መሬት በሚሉ ከእውነታው ጋር የማይገናኙ ነገሮችን እያገናኘ የስም ማጥፋት ዘመቻውን በስፋት ቀጥሎበት ይገኛል፡፡ እ.ኤ.አ ዴሴምበር 2011 (“ኢትዮጵያ፡ ፍርኃት እና ስም የማጥፋት ዘመቻ” እና እ.ኤ.አ ፌብሯሪ 2013) የኢትዮጵያን ሙስሊሞች መብት በመከላከል የባለስልጣኖች በእምነት ላይ ጣልቃ የመግባት፣ የመፐወዝ እና አግባብ ያልሆነ የቁጥጥር ስርዓት እንዲወገድ ተከራክሪያለሁ፡፡
የወያኔ የወሮበላ ስብስብ አሁን በህይወት የሌለውን የመለስ ዜናዊ የሌለውን እውነተኛ ያልሆነውን ስብዕና በቅጥፈት እና በዘራፊነት ስብዕና ለመተካት ሲባል የዳግማዊ ምኒልክን ሰብዕና ሲቆርጡ እና ሲቀጥሎ ተመልክቻለሁ፡፡ ይህንንም ጉዳይ በማስመልከት “የኢትዮጵያን ታሪክ ጥላሸት መቀባት” በሚል ርዕስ ባቀረብኩት ትችት በምንመጣበት ጊዜ በዓላማ ጽናት (ነገሮችን በጥንቃቄ የመያዝ እና ልዩ የሆነ ውስጣዊ ባህሪ)፣ ያቀዱትን እና ያሰቡትን ከመፈጸም አንጻር (የተግባር ሰው፣ ታማኝ)፣ ክብር ከመስጠት አንጻር (በክብር መሞላት እና እራስን ምሳሌ አድርጎ ሌሎችን የመሳብ ሁኔታ) እና ልዩ ተፈጥሯዊ ባህሪ (አንድን ጉዳይ ለመፈጸም በጦርነት ጊዜ የሚታይ ጅግንነት፣ ጽናት፣ ደፋርነት) በሚታይበት ጊዜ መለስ ከምኒልክ ጋር መወዳደር ቀርቶ የጫማቸው ተረከዝ የማይደርስ በወያኔ የይስሙላ ዲስኩር ታጅቦ ለእኩይ ዓላማ ማራመጃቸው ሲባል ብቻ ፕሮፓጋንዳ የሚነዛለት ቀፎ መሆኑን ለማሳየት ሞክሪያለሁ፡፡ መለስ እና ግብረ አበሮቹ ከምርጡ ከእምዬ ምኒልክ ጋር (ስማቸው በምግባራቸው እና በተግባራቸው በሚወዳቸው ህዝብ ፍላጎት የተሰጠእንጅ እንደ መለስበጉልበት ፕሮፓጋንዳ በህዝብ ላይ ለመጫን ያልተሞከረ መሆኑን ልብ ይሏል) ሊወዳደሩ የማይችሉ ተራዎች መሆናቸውን ለማሳየት ጥረት አድርጊያለሁ፡፡ ምኒልክ በአመራር ጥበባቸው ከፍተኛውን ስኬት የተጎናጸፉ ክብር ያላቸው መሪ ነበሩ የሚለውን ለማረጋገጥ የሚጠበቅብኝ አይሆንም፡፡ (እ.ኤ.አ ኖቬምበር 7/1909 በኒዮርክ ታይምስ ታትሞ የወጣውን መመልከት በቂ ነው፡፡)
እንደዚሁም ሁሉ የወያኔ ወሮበላ ስብስብ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲ ቡድን አመራሮችን፣ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾችን እና ሌሎችን ለሀገር የሚቆረቆሩ ዜጎችን ለማዋረድ ሲሉ ሁሉንም ዓይነት የጅልነት ተግባራት፣ ኃላፊነት የማይሰማው የህጻናት ዓይነት ድርጊቶችን በአደባባይ ስፈጽሙ ይታያሉ፡፡ ከጥቂት ዓመታት በፊት ታላቁን የመድረክ ላይ ተውኔት ባለሙያ ቀንዲል የሆነውን ደበበ እሸቱን እንደ አንዳርጋቸው ጽጌ ሁሉ በእስር ቤት ውስጥ አስገብተው የውሸት ድሪቶ የቪዲዮ ፊልም ቀረጻቸውን አዘጋጅተው ግብር በሚከፈልበት በኢትዮጵያ ህዝብ ቴሌቪዥን በማቅረብ ለህዝብ ህሊና ለፍርድ ሲያቀርቡት እርሱን ያዋረድን መስሏቸው እነርሱ እራሳቸው በቅሌት እና በውርደት ጉድጓድ ውስጥ ወደቁ፡፡ ያንን የማይረባ እርባናየለሽ የቪዲዮ ፊልም ዘገባ ከተመለከትሁ በኋላ የእራሴን የህሊና ፍርድ ሰጥቸ ነበር፡፡ ለአርቲስት ደበበ እሸቱ ከፍተኛ የሆነ አድናቆት እንዳለኝ እና ታላቅ ክብርንም በመስጠት የህሊና ፍርድን የበየንኩት ለዓላማው በጽናት የቆመ መንፈሰ ጠንካራ ስለሆነ ብቻ አልነበረም ሆኖም ግን እውነተኛ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ጀግናም ስለሆነ ጭምር እንጅ፡፡ ደበበ እሸቱ ለሰብአዊ መብት ጥበቃ እራሱን መስዋዕት ያደረገ ኢትዮጵያዊ እንደሆነ አውቃለሁ፡፡
የወያኔ የወሮበላ ስብስብ የኢትዮጵያ የሙስሊም ማህበረሰብ የሰብአዊ መብት ተሟጋች በሆነው በአቡባከር አህመድ ላይ ተመሳሳይ ድርጊትን ፈጽሟል፡፡
የወያኔ ወሮበላ ስብስብ በአንዳርጋቸው ላይ የተለየ ድርጊት አልፈጸመም፡፡ በተለየ ቀን እና በተለየ የሰብአዊ ፍጡር ሰለባ ላይ የተገበረው ከመሆኑ በስተቀር የወያኔው ስብስብ ያው የተለመደውን ‘የሞኝ ዘፈን ሁል ጊዜ አበባዬ’ የሚለውን ዘፈንበመዝፈን እስክስታውን በማስነካት ላይ ይገኛል፡፡ እስክስታው እስከ መቼ ይዘልቃል የሚለው ወደፊት የሚታይ ይሆናል!
በማይታወቅ ጊዜ፣ ቦታው የት እንደሆነ በማይታወቅ አካባቢ ተቆርጦ እና ተቀጥሎ በተዘጋጀው የወያኔ የቪዲዮ ቀረጻ ላይ የኢትዮጵያ ህዝብ ሰምቶ እና ተመልክቶ የእራሱን የህሊና ፍርድ እንዲሰጥ ሲጋበዝ ለጊዜው የሚደረገውን ጉድ ከመመልከት በስተቀር ምንም ዓይነት ነገር ሳልናገር ዝም ብየ ቆይቻለሁ፡፡ ምንድን ነው የሚያስቡት የነበረው? (ያ የደንቆሮ ጥያቄ ነው፡፡ ምንም አያደርጉ! እንደዚህ ያለ እርባናቢስ የሆነ የቪዲዮ ፊልም ተዘጋጅቶ እንዲለቀቅ ያደረገው ማን ነው? (እንደገና ሌላ የደንቆሮ ጥያቄ፡፡) የወያኔ ወሮበላ ስብስብ በእኛ ብልህነት ላይ ያለው ንቀት እኛ በወያኔ ድንቁርና፣የአዕምሮ ዘገምተኝነትእና ድድብና ላይ ያለን ንቀት ብቻ ይበልጠዋል ። አንድ ሰው በሰጠው ምላሽ ብቻ በመመርኮዝ የህሊና ዳኝነት እንድንሰጥ ይጠይቁናል! እንግዲህ ይህ ምን አይነት የደንቆሮና በድን አስተያየት ነው!
አንዳርጋቸውን በቃሎቻቸው ሳይሆን በሰጧቸው ምላሾች መገምገም፣
የአንዳርጋቸው ጠያቂዎች የጠያቂዎቹን ማንነት፣ የት ቦታ እንደሆነ እና የቪዲዮ ፊልሙ መቸ እንደተቀረጸ፣ እንዲሁም አንዳርጋቸውን ለማዋረድ ከፍተኛ የሆነ የመድረክ ላይ የሸፍጥ ትወና በማካሄድ የተዛባ፣ የተዛነፈ፣ የተንሸዋረረ እና የተፐወዘ ውጤት በህዝቡ ላይ ለመፍጠር በሚል እኩይ ድርጊት አጠቃላይ ሁኔታውን ለመደበቅ ጥረት አድርገዋል፡፡ ሆኖም ግን አንዳርጋቸው ሰጧቸው በተባሉት ምላሾች ላይ ታሪኩን በተለየ መልኩ ሊያሳዩ የሚቸሉ ሌሎች ምላሾች ነበሩ፡፡
የቪዲዮ ቀረጻ ወንጀልን በሚያጠኑ እና በሚከላከሉ ባለሙያዎች ትንትና መሰረት ትንሽ ነገር ማለት ይቻላል፡፡ የአንዳርጋቸውን የሰውነት አጠቃላይ እንቅስቃሴ፣ ውሱን የሆኑ የአካላቸውን ንቅናቄ እና በቪዲዮ የቀረጻ ክፍሎች ሂደት ጊዜ የተደረገውን የሰውነታቸውን አቀማመጥ በአንክሮ በመመልከት ብቻ ጠቃሚ የሆኑ መረጃዎች እንዳሉ ይገልጻሉ፡፡ ያም ሆነ ይህ በወያኔ የወሮበላ ስብስብ ተቀርጾ በተለቀቀው የቪዲዮ ፊልም ምላሾች ላይ በርካታ የሆኑ እርስ በእርስ የማይገናኙ እና የተጣረዙ ውዥንብሮች በገፍ ታጭቀው ይታያሉ፡፡ የወያኔ የወሮበላ ስብስብ የቪዲዮ ቀረጻ እንደሚያሳያው አንዳርጋቸው ከብዙዎቹ በጥቂቶቹ ጣቶቻቸውን ሲያወናጭፉ ይታያሉ፣ አዲስ የሆነ ያልተለመደ የሰውነት እንቅስቃሴ ያሳያሉ፣ እጆቻቸውን በአየር ላይ ከወዲያ ወዲህ ያወናጭፋሉ፣ እራሳቸውን በተደጋጋሚ ያወዛውዛሉ፡፡ አቶ አንዳርጋቸው በወያኔው የማጎሪያ እስር ቤት ከመግባታቸው በፊት በሚታወቁ አጋጣሚዎች እና በህዝብ ፊት ንግግር ሲያደርጉ የተቀረጸውን አጠቃላይ የሰውነታቸውን እንቅስቃሴ አሁን ከተቀረጸው የሸፍጥ የቪዲዮ የመድረክ ላይ ትወና ቀረጻ ጋር ሲነጻጸር በአጠቃላይ በወያኔ ይዞታ ስር ሆኖ የሚያደርገው እንቅስቃሴ ሁሉ አዲስ እና ያልተለመደ መሆኑን በግልጽ ያመላክታል፡፡
በወያኔ የቪዲዮ ቀረጻ በርካታ ክፍሎች ላይ የአንዳርጋቸውን የሰውነት አቀማመጥ፣ እንቅስቃሴ እና አጠቃላይ ሁኔታ በምንመረምረርበት እንዲሁም ምላሾቻቸውን በሚሰጡበት ጊዜ የሚታይባቸው የመረበሽ ሁኔታ እርሳቸው በከባድ ውጥረት ውስጥ እና በከፍተኛ ጭንቀት ውስጥ መሆናቸውን በግልጽ ያለመላክታል፡፡ የተወሰኑ “ምላሾች” የተለዩ ከፍተኛ የሆኑ ጭንቀቶችን መዝግበው ይታያሉ፡፡ አጠቃላይ የሰውነታቸው ገጽታ በንቀት የሚመለከቷቸውን ጠያቂዎቻቸውን በማየት እንዲሁም በእርሳቸው ላይ የጥላቻ መንፈስን ከሚያሳዩ ጠያቂዎቻቸው ጋር ዓይን ለዓይን ሲተያያዩ መንፋሳቸው እየተረበሸ አስደናቂ በሆነ መልኩ ገጽታቸው ሲለዋወጥ በግልጽ ይታያል፡፡ አንዳርጋቸው በተቀመጡበት ወንበር ላይ ሆነው በርካታ የሆኑ የተጋነኑ የሰውነት ገጽታዎችን እና የሰውነት እንቅስቃሴ ምልክቶችን አንዴ ኮስተር በማለት ሌላ ጊዜ ደግሞ ፈታ በማለት ያልተለመደ እና ከፍተኛ የሆነ የአካል እና የመንፈስ ምቾት የሌላቸው መሆኑን በግልጽ ያመላክታል፡፡
አንዳርጋቸው ምላሾችን በሚሰጡበት ጊዜ የድምጻቸውን መጨቆን እና በተለመደው ሁኔታ መናገር አለመቻላቸው፣ ምላሾችን ብቻ እንዲናገሩ የተሰጧቸው መሆኑን እንዲሁም ድምጻቸው በጣም የደበዘዘ እና የሰነነ መሆኑን ስናጤን ለሚሰጧቸው ምላሾች እና መግለጫዎች ሁሉ በግዳጅ እንዲመልሱ መደረጋቸውን በግልጽ ያመላክታል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የአንዳርጋቸው ምላሾች ድንገተኛ እና ወዲያውኑ ከሚቀርቡት ጥያቄዎች በመነሳት የሚሰጡ አይደሉም፣ ሆኖም ግን ቀደም ሲል የተዘጋጀ እና ይህንን ለማድረግ ሲለማመዱት የቆየ ይመስላል፡፡ የአንዳርጋቸው በቡርጅ አል መለስዜናዊሆቴል የንጉሳዊ ቤተሰብን የመሰለ እንክብካቤ እንደሚደረግላቸው ሆኖ የቀረበው የማይታመን መሆኑ ብቻ አይደለም ሆኖም ግን በማያስፈልግ ሁኔታ እጅግ ተጋንኖ የተዘጋጅ የመድረክ ትወና ነው፡፡
የአንዳርጋቸው የድምጻቸው ቅላጼ ከፍ እና ዝቅ የማለት ሁኔታ እንደዚሁም የተወሰኑ ቃላት እና ሀረጎችን በሚናገሩበት ጊዜ የድምጽ መቀያየር ሁኔታ ለጠያቂዎቻቸው ምላሽ በሚሰጡበት ጊዜ ከሚኖርባቸው ጭንቀት የተነሳ የተፈጠሩ ሊሆኑ እንደሚችሉ ለመገመት ይቻላል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ሲያሳዩትየነበረው የሰውነት እንቅስቃሴ ከአፋቸው ከሚወጣው ድምጽአንጻር ሲታይ በጣም ወደ ኋላ የተጓተተ የመሆኑ ጉዳይ በድምጻቸው እና በአካላዊእንቅስቃሴ መካከል የመጣጣም ሁኔታአለመታየቱን ያመላክታል፡፡
አጠቃላይ በሆነ መልኩ ስናየው አንዳርጋቸው ከሚሰጧቸው እንደ ደኃ ከረጢት ከተጣጣፉት የቪዲዮ ቀረጻ ምላሾች አንጻር በመነሳት ስናየው በጣም ውጥረት የበዛበት ሁኔታ ውስጥ ሆነው ተገደው የሰጡት መሆናቸውን በግልጽ ያመለክታል፡፡ ውስን ለሆኑ ምላሾች አንዳርጋቸው የሚሰጧቸው ምላሾች ጭንቀት፣ ያለመረጋጋት፣ ተጠራጣሪነት፣ ፍርሀት፣ ንዴት እና እንዲሁም የመሰላቸት ሁኔታ ይታያል፡፡
አንዳርጋቸው በእርግጥ ለወያኔ ቪዲዮ በትክክል ምላሾችን በመስጠት ሀሳባቸውን ለመግለጽ ወይም ደግሞ ለመድረክ ትወና ፍጆታ ሲባል ብቻ ምላሽ ሊሰጡ ይችላሉን? አንዳርጋቸው እንዲናገሯቸው ከቀረቡላቸው ምላሾች ውጭ እራሳቸው የሚያምኑበትን መልስ ሊሰጡ ይችላሉን? ለእነዚህ ጥያቄዎች የሚሰጡትን መልሶች አውቃለሁ፣ ሆኖም ግን አንባቢዎቼ ሁሉ የእራሳቸውን የህሊና ፍርድ እንዲሰጡ እጠይቃለሁ፡፡
የወያኔ ወሮበላ ስብስብ ለሚቀጥለው ጥያቄ አልባ የቪዲዮ ምላሽ ዝግጅቱ የሚከተሉትን በጣም ቀላላ የሆኑ የቪዲዮ ምስልምርመራ ዘዴዎችን በመጠቀምለህዝብ “የህሊና ፍርድ” ያቀርባል የሚል ተስፋ አለኝ፡፡
አንዳርጋቸው ማራኪዎቻቸውን እንዲወዱ የተገደዱ የስቃይ ሰለባ ናቸውን?
የቪዲዮ ምስል ምርመራ ትንታኔ ባለሙያዎች እንደሚሉት አንዳርጋቸው ‘ማራኪን በመገደድ መውደድ’ (አስቶክሆልም ስንድሮም) እየተባለ ለሚጠራው የምርኮ ሰለባ የሆነው ወይም ደግሞ ምርኮኛው ማራኪውን እንዲወድ የሚዳረግበት የስነልቦና ክስተት ሰለባ ውስጥ ወድቀው ሊሆን ይችላል፡፡ የዚህ ዓይነት ክስተት ሰለባ የሆኑ ሰዎች ብዙውን ጊዜ የሌሎችን ስሜቶች እና ፍላጎቶች በማወቅ እና በአሳሪው/ዋ ላይ ፍቅርን በማሳየት አሳሪውን/ዋን ከመጥፎ ነገር ለመከላከል በማሰብ የተወሰኑ አዎንታዊ የሆኑ እና ሞቅ ያሉ ስሜቶችን ግልጽ ማድረግ ይጀምራሉ፡፡ ሰለባዎቹ አንደ ደግ እና ጨዋ ሰው ሆኖ ምንም ዓይነት የሰብአዊ መብት ረገጣ ያልተፈጸመበት ለምመሰል ከሰውነት እንቅስቃሴዎቹ ጋር እኩል ትርጉም የሚሰጥ መስሎ ሊቀርብ ይችላል፡፡ በቪዲዮው የቀረበው የአንዳርጋቸው የመጨረሻው ምላሽ ተገዶ ማራኪን በመወደድ ደረጃ የስነልቦና ክስተት ውስጥ መግባታቸውን የሚያመላክት ሊሆን እንደሚችል ጠንከር ያለ ጥርጣሬን ይሰጣል፡፡
የህዝብ መገናኛ የመድረክ ተውኔቱ ይቀጥል…
የወያኔ ወንድሞች የባለ ሶስት ቀለበት መድረክ ላይ ተውኔት ይቀጥል፡፡ ቀለበት አንድን በእስክንድር ነጋ፣ በርዕዮት ዓለሙ እና በውብሸት ታዬ፣ ቀለበት ሁለትን ደግሞ በአንዷለም አራጌ እንዲሁም ደግሞ ቀለበት ሶስትን በበቀለ ገርባ እና በአቡባከር አህመድ ላይ ይተወኑበት፡፡
በአንዳርጋቸው ጽጌ ላይ በቀረበው አስከፊ እና ፍትሀዊነት የጎደለው የእስር ቤት አያያዝ እና የቪዲዮ ቀረጻ የመድረክ ላይ ተውኔት ያለኝን የህሊና ፍርድ ሰጥቻለሁ፡፡ ሁሉም አንባቢዎቼ ይህንኑ ተመሳሳይ ድርጊት እንዲፈጽሙ በአክብሮት እጠይቃላሁ፡፡ ፍርድ ከመስጠት በፊት እንዲህ የሚለውን አንድ ጥያቄ አንባቢዎቼ እንዲመልሱልኝ እጠይቃለሁ፡ በአንዳርጋቸው የተሰቃዩ ቃላት ወይስ ደግሞ በአንዳርጋቸው የተሰቃዩ የሰውነት እንቅስቃሴዎች ላይ ነው እምነት የሚኖራችሁ?-
በቪዲዮ ቀረጻ ምስል ትንተና ለዲጂታል የብዙ መገናኛ መሳሪያ ቴክኖሎጂ የስራ መስክ ድጋፍ ለሚያደርጉ የስራ ባልደረቦች ምስጋና ይሁን!

ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!

ከሆቴሉ ጀርባ… በወላፈኑ ውስጥ የሚታየው – ፍጹምዘአብ አስገዶም ማን ይሆን?

ዘ-ሐበሻ 

  • 1637
     
    Share
bee392ccb91b968f78a29a035271c5d5_Lሰሞኑን የኢትዮጵያ ጥንታዊ ቅርስ የነበረው ጣይቱ ሆቴል በእሳት ወደመ:: ከዚሁ ጋር ተያይዞ ታዲያ “አቃጠሉት” እና “አቃጠሉበት” የሚሉት ድምጾች በርክተዋል:: “አቃጠሉበት” የሚለውን የጨዋታ ክር መምዘዝ ከጀመርን; የቤቱ ባለቤት ፍጹምዘአብ ጋር ያደርሰናል:: ፍጹምዘአብ የትግራይ ተወላጅ ነው:: ግን ደግሞ የትግራይ ተወላጅ ስለሆነ ከስልጣን ዙፋን ላይ አልተቀመጠም:: ይልቁንም በዘመነ ኢህአዴግ ከ6 አመታት በላይ የወያኔን እስር ቤትን ቀምሶ የወጣ ሰው ነው::
አሁን በተቃጠለው የጣይቱ ሆቴል ምክንያት ስለቃጠሎውም ሆነ ስለእቴጌ ጣይቱ ሆቴል ብዙ እየተባለ ነው:: ከዚህም በላይ ብዙ ሊባል ይችላል:: ምንም ተወራ ምን – ቢያንስ መሰረቱን እውነት ያደረገ ወሬ ይመረጣል:: ፍጹምዘአብ የትግራይ ተወላጅ ሆኖ የህወሃት ደጋፊም ተቃዋሚም ስላልሆነ እንደማንፈርድበት ሁሉ – የነጻ ፕሬስ ተጋድሎውን ብዙ በመታሰር እና ባለመታሰሩ ኢትዮጵያዊነቱን ልንለካው አንችልም:: እንደ’ውነቱ ከሆነ; ዘ ሞኒተር ጋዜጣን በሳምንት ሶስቴ ከመታተም አልፎ በየቀኑ የሚታተም የመጀመሪያ እንግሊዘኛ ጋዜጣ እንዲሆን አድርጓል:: ጋዜጣው ከዘመኑ ጋር እንዲሄድ ብቻ ሳይሆን የራሱ ማተሚያ ቤት እንዲኖረው ማድረጉ በራሱ፤ መጋነን ባይገባውም በነጻው ፕሬስ ታሪክ ውስጥ ስፍራ ሊሰጠው ይገባል::
(ዳዊት ከበደ ወየሳ)
ፍጹምዘአብን የምናውቀው ከመጀመሪያዎቹ የኢትዮጵያ ነጻ ፕሬስ ጋዜጦች አንዱ የሆነውን “ዘ ሞኒተር” ጋዜጣ አሳታሚ ሆኖ ሲሰራ ነው:: እኛ የነጻው ፕሬስን የነጻነት ብዕር ይዘን ባማርኛ ስንውተረተር – ፍጹምዘአብ በእንግሊዘኛ የሚታተም ዘሞኒተር ጋዜጣን ተረጋግቶ ያሳትም ነበር:: የነበረውን መንግስት የሚቃወም ወይም ያለፈውን የደርግ ስርአት የሚያወግዝ ጽሁፍ እምብዛም በጋዜጣው ላይ አይነበብም:: ሁሉንም ነገር በጥንቃቄ ለመያዝ ይሞክራል:: ከዚህም ከዚያም ጋር እየሄደ አይላተምም:: እኛ ኢህአዴግ ያጠመደውን የፕሬስ ነጻነት አልፈን፤ ፈንጂ ወረዳውን እየረገጥን ስንረጋገጥ – ፍጹምዘአብ ግን በጩኸት እና በትርምሱ መሃል በጥንቃቄ መራመድን ያዘወትር ነበር:: እንደዛም ሆኖ ግን ከህወሃት ሰዎች የጥላቻ አይን ሊወጣ አልቻለም::
የኢትዮጵያ ነጻ ፕሬስ ጋዜጠኞች ከየቢሯቸው እየተለቀሙ ከታሰሩባቸው ጊዜያት መሃል፤ የፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ እና አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የተነሳው አመጽ ጉዳይ ይጠቀሳሉ:: (እ.ኢ.አ. 1984 እና 1985)
በዩኒቨርስቲው ዘገባ ጉዳይ እኔም ተከስሼ ጉዳያችን ከነሙሉጌታ ሉሌ እና ከነመጽሃፈ ሲራክ መዝገብ ጋር በጠቅላይ ፍርድ ቤት ችሎት ይታይ ነበር:: ይሄ የአንድ ሰሞን ወሬ እንዳለፈ ደግሞ ሌላ ዙር ወሬ መጣ – በዙምባብዌ ኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማርያም ላይ የተደረገው የመግደል ሙከራ የፕሬሱን ገጾች አጣበበ::
በዚህ አዲስ የወሬ ዙር የነፍጹምዘአብ ዘ ሞኒተር ጋዜጣ የፕሬሱን የፈንጂ ወረዳ ረገጠ:: እናም ለሁሉም ጋዜጠኛ የተዘጋጀውን እስር ቤት አብሮን ለመጋራት በቃ – 1988::
ይህ እስር በጥንቃቄ መራመድ ለሚያዘወትረው ፍጹምዘአብ አስገዶም የማንቂያ ደወል ነበር:: እዚህ ላይ ዝርዝሩ ጥቅም የለውም እንጂ አስቀድማ የታሰረችው የጋዜጣው አዘጋጅ ሉሊት ነበረች:: እሷ ወሬውን የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ኢቲቪ እና ሬድዮ ጭምር መዘገቡን ለመርማሪው ታስረዳለች::
መርማሪው መልሶ ይጠይቃታል “እኮ አንቺ ዜናውን ከየት አገኘሽው?”
“ኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ካገኘበት ነዋ”
“ማነው ኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት?”
ሉሊት ማስረዳቷን ቀጠለች፤ “የመንግስት ዜና አገልግሎት ነው:: እነሱ ዜናውን ከፓን አፍሪካ ኒውስ እና አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ነው ያገኙት:: እኛም እንደነሱ ወርሃዊ ክፍያችንን ስለምንፈጽም የፓናፍሪካ እና የአጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዜናዎች ይደርሱናል” …ሉሊት እና መርማሪው ሊግባቡ አልቻሉም:: እንዲያውም መርማሪው ከአቅሙ በላይ ስለሆነበት ጉዳዩን ለበላይ ሃላፊዎቹ አስተላለፈ:: የበላይ ሃላፊዎች ደግሞ የጋዜጣው አሳታሚ ፍጹምዘአብ ተጨምሮ እንዲታሰር አደረጉ – ያን ግዜ እሱ እና እኛ በእስር ቤት እኩል ሆንነ :)
ያኔ የፍጹምዘአብ እድሜ ገና በሰላሳዎቹ መጀመሪያ ላይ ስለነበር እድሜያችን ሃያ + ለነበርነው እንደታላቅ የሚታይ ነው:: ለነገሩ በሁኔታው የራዕይ ገንቦ ተሸክሞ የሚሄድ ይመስላል። በዚያን ኢንተርኔት እና ማህበራዊ ድረ ገጾች በኢትዮጵያ ቀርቶ በአፍሪቃ ባልተስፋፋበት ዘመን እሱ ከዘመኑ ጋር ለመራመድ ዳዴ ማለቱን ጨርሷል:: እኛ በሳምንት አንድ ጊዜ የምናሳትማት ጋዜጣ በአፈና ጫና ስር ሆና ስትንፈራፈር – እሱ ወደፊት በኢትዮጵያ የህትመት ብቻ ሳይሆን፤ የግል ኤሌክትሮኒክስ መገናኛዎች መስፋፋት እንዳለባቸው ጥልቅ ትንታኔ ይሰጥ ነበር:: ሆኖም ያቺ አጭር የእስር ዘመን ፍጹምዘአብ አይኑን ገልጦ በኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን የህወሃት አምባገነን ስርአት እንዲመለክት የረዳው ይመስላል::
ታሪኩን ለማሳጠር ያህል ሉሊትም ሆነች ፍጹምዘአብ በኋላ ላይ በአስር ሺህ ብር ዋስ ሲወጡ ጋዜጣቸው ለአንድ ወር ያህል ከህትመት ታግዶ ነበር:: በቀጣይ ግዜያቶች… ዘ ሞኒተር ጋዜጣ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ጉዳዮችን እንደጾመ ቀጠለ:: ሆኖም በሚገርም ሁኔታ የነጻ ፕሬስ ጋዜጠኞች ሲታሰሩ ጉዳያቸው በውጭ ቋንቋ ተመንዝሮ የሚጻፍበት ብቸኛው እንግሊዘኛ ጋዜጣ ዘ ሞኒተር እንደነበር በፕሬስ ጉዳይ ታስረን የወጣን ሰዎች ሁሌም የምናስታውሰው ነው:: በኋላ ላይ እንደሰማሁት… ሌሎች ጋዜጠኞች ዲ አፍሪክ ጋር በነበረው አርቲክራፍት በተባለ ማተሚያ ቤቱ ያውቁታል – ያመሰግኑታል::
ጋዜጣም ሆነ መጽሄት ለማሳተም ወደዚህ ማተሚያ ቤት የሄድንበት አጋጣሚ የለም:: ሆኖም የኋላ ኋላ የመንግስት ማተሚያ ቤቶች ሲያስቸግሩ የነጻው ፕሬስ ልጆች ወደዚህ ማተሚያ ቤት ሄደው ያሳትሙ እንደነበር – በቅርቡ ከወጡት ጋዜጠኞች መካከል ሰርካለም ፋሲል አስታውሳኛለች::
ፍጹምዘአብ አስገዶም ብዙ የማያወራ ብቻ ሳይሆን በአደባባይ ልታይ ልታይ ማለትን የሚያዘወትር አይደለም:: ውስጡ ሁልጊዜም በዝምታ የተወጠረ እና መቼ እንደሚፈነዳ በማይታወቅ እሳተ ጎመራ የታመቀ ነው:: በዚህ የሰከነ ስሜት ውስጥ ያለ ሰው በፖለቲካ ምህዋር ዙሪያ ሊሽከረከር ቀርቶ – በዚያ ዙሪያ የሚሽከረከሩትንም በሩቁ ከማየት ውጪ እምብዛም ተሳትፎ አያደርግም:: ነገር ግን ምንም ቢጠነቀቅ የፖለቲካው በትር አናቱን ሳይመታው አያልፍም። ምንም ስሙን እና ማንነቱን ቢደብቅ – ማን እንደለኮሰው በማይታወቅ የእሳት ወላፈን መሃል በጭላንጭልም ቢሆን እናየዋለን – ፍጹምዘአብ አስገዶምን::
እንግዲህ ነገሮች በዚህ አይነት አለፉና መታሰር አይቀርም – በ5ኛ አመቱ እንደገና የሚታሰርበት ጊዜ መጣ። በነስዬ አብርሃ ላይ ጥርስ የነከሰው ህወሃት – የነሱ ተባባሪ ያላቸውን ሰዎች በሙስና ሰበብ ማሰር ጀመረ። የሙስናው ምንጭ የተባለው ደግሞ የአቶ ስዬ አብርሃ ታናሽ ወንድም “አሰፋ አብርሃ” መሆኑ ነገሩን ከፍ አደርገው። እኛ በጋዜጣችን ላይ የአቶ አሰፋ አብርሃን የሙስና ጉዳይ ስናነሳ፤ “የክቡር አቶ አሰፋ አብርሃን ስም በማጥፋት…” ተብሎ፤ አንቀጽ ተጠቅሶ፤ እውነት መናገር ወንጀል ሆኖ፤ መንግስት በፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 1ኛ ችሎት ከሰሰን። በሚገርም ሁኔታ ግን… የኛ ፋይል ሳይዘጋ አቶ አሰፋ አብርሃን መንግስት ራሱ ከሰሳቸው። ይህን እንደምሳሌ ማንሳት ያስፈለገው – ሰው የኢህአዴግ መንግስት ደጋፊ እስከሆነ ድረስ በሙስና ጭቃ ውስጥ ተዘፍቆ መኖር ይችላል። ከመንግስት ጋር የሚያጣላውን ነገር ከሰራ ግን፤ ስሙ በጥቁር መዝገብ ላይ ሰፍሮ ወደ እስር ቤት ይወረወራል።
ፍጹምዘአብ አስገዶም በፕሬሱ ውስጥ ያደረገው አስተዋጽኦ እንዳለ ሆኖ የትዳር እና የንግድ ህይወቱን በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ ከነአሰፋ አብርሃ ጋር አቆራኝቶታል። በአንድ በኩል የፍጹምዘአብ ባለቤት የአሰፋ አብርሃ ታናሽ እህት ናት። በሌላ በኩል ደግሞ ጨረታ እያሸነፈ ያገኛቸው የንግድ ቦታዎች በአሰፋ አብርሃ ፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ የተሸጡ የቀድሞ መንግስት ንብረቶች ናቸው። እነዚህም የጉለሌ ሳሙና ፋብሪካ፣ የሃረር ማተሚያ ቤት እና የጣይቱ ሆቴል ናቸው። ከሁሉም ግን የጣይቱ ሆቴል ጉዳይ ጎልቶ በነጻው ፕሬስ ላይ የመነጋገሪያ አጀንዳ ሆኖ ሰንብቶ እንደነበር ብዙዎች እናስታውሳለን።
ፍጹምዘአብ አስገዶም ጣይቱ ሆቴልን የገዛው በ425 ሺህ ብር ሲሆን፤ በወቅቱ ብቸኛው ተጫራች ሆኖ ነበር ጨረታውን ያሸነፈው። የተገዛበት ዋጋ ዛሬም ድረስ እንደአስደናቂ ታሪክ መወራቱ ቀጥሏል። ምክንያቱም እንኳንስ ጣይቱ ሆቴል ከነግቢው ቀርቶ፤ በሆቴሉ የላይኛው ክፍል ውስጥ ያለው በ19ኛው ክፍለዘመን ዝነኛ የነበረው የ1889 ስቴንዌይ ፒያኖ ግማሽ ሚሊዮን ብር ያወጣልና። ይህም ሆቴሉ ከተገዛበት ዋጋ ጭምር ያነሰ ነው። እናም ይህ ለማመን የሚያስቸግር ዋጋ – ለፍጹምዘአብ እንደሎተሪ ማሸነፍ የሚቆጠር ነበር። በወቅቱ ነጻው ፕሬስ ውስጥ ያለነውም ሆንን ባህል ሚንስቴር ውስጥ ያሉ አንዳንድ ሰዎች፤ “ጣይቱ ሆቴል በቅርስነት መጠበቅ ያለበት እንጂ፤ ሊሸጥ የሚገባው ንብረት አይደለም።” ብለው እና ብለን ድምጻችንን አሰማን። ሆኖም የሚሰማን ጠፍቶ ጣይቱ ሆቴል ተሸጦ እ.ኢ.አ. ሰኔ 21 1991 ዓ.ም. ርክክቡ ተፈጸመ – የኛም ጩኸት የአንድ ሰሞን ጫጫታ ሆነና ሁሉም ነገር ከግዜው ጋር ተረሳ።
ይሄ ጩኸት ሌላ ትርጉም እስካልተሰጠው ድረስ የቅናት እና የምቀኝነት አልነበረም። ሰሚ ጠፋ እንጂ… ጩኸታችን የኢትዮጵያን ቅርስ ከመጠበቅ አንጻር የሚታይ ነው። ጣይቱ ሆቴል ጥንታዊነቱን ጠብቆ በቅርስነት መጠበቅ ሲገባው እንደሸቀጥ መሸጥ አይገባውም ነበር – የኛ ክርክር። እርግጥ ነው – ጉለሌ ሳሙና ፋብሪካን ከ22 ሚሊዮን ብር በላይ ጨረታ አሸንፎ፤ ከአንድ አመት በፊት ለገዛው ፍጹምዘአብ የጣይቱ ሆቴል ዋጋ አነስተኛ መሆኑ ጥያቄ ውስጥ የሚገባ አይደለም። ሌላው ቀርቶ አሁን ጣይቱ ሆቴል ሲቃጠል የጃዝ-አምባ የሳውንድ ሲስተም እና የሙዚቃ መሳሪያ አብሮ ወድሟል። ስራ አስኪያጁ ኤርሚያስ ፋንቱ እንዳለው ከሆነ፤ “በትንሹ የ4 ሚሊዮን መሳሪያ በቃጠሎው ጠፍቶብናል” ብሏል። ጣይቱ ሆቴል የተገዛበትና የጠፋውን ንብረት ስናነጻጽረው… “የስሙኒ ዶሮ የአንድ ብር ገመድ ይዛ ጠፋች” የሚባለውን ተረት ያስታውሰን ጀምሯል።
ነገርን ነገር እየመዘዘ ወደ ታሪኩ ማጠቃለያ ልንቃረብ ሆነ። ወደኋላ እንመልሳችሁ እና አንዳንድ ነጥቦችን እናንሳ። በዛው ከላይ የጀመርነውን ጨዋታ መስመር እናስይዘው።
…ከዛ በኋላ… ስዬ አብርሃ ከነመለስ ዜናዊ ጋር ስለተጣላ በሙስና ሰበብ ታሰረ። ታናሽ ወንድሙ አሰፋ አብርሃ – በጠቅላይ ሚንስትርነት ማዕረግ – የፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ ሃላፊ እና የንግድ ባንክ ቦርድ ሰብሳቢ ሆኖ ሲሰራ፤ የፈጸመው ሙስና አለ ተብሎ እሱም ታሰረ። ፍጹምዘአብም “ከአሰፋ አብርሃ ጋር ያለውን ግንኙነት በመጠቀም ጉለሌ ሳሙናን፣ ሃረር ማተሚያ ቤት እና ጣይቱ ሆቴልን ገዝቷቸዋል” የሚል ክስ ተመሰረተበት።
እርግጥ ነው። ፍጹምዘአብ ከመታሰሩ በፊት… ጣይቱ ሆቴልን እያደሰው ነበር። ከታች ለደንበኞች አገልግሎት ይሰጥ የነበረው ቦታ እንዳለ ነው። ከሱ በላይ የነበረው ፎቅ ደግሞ የቀድሞ ሰራተኞች ያድሩበት የነበረ ስፍራ ነው። በኋላ ላይ… እድሳት አድርጎ፤ የፎቁን ቦታ ለእስዕል ጋለሪ እንደሚጠቀምበት ስንሰማ “ይሁን” አልነ። ፍጹምዘአብም ቢሆን ቢሮውን እዚሁ ጣይቱ ሆቴል አድርጎ፤ በየእለቱ የሚወጣውን የዴይሊ ሞኒተርን ጉዳይ የሚከታተለው ከዚሁ ከጣይቱ ሆቴል ሆነ። ሆኖም ሆቴሉንም በገዛው በ2ኛው፤ ጋዜጣውም በተመሰረተ በ10ኛ አመት ታሰረ።
በሚገርም ሁኔታ… ፍጹምዘአብ የታሰረው ከአሰፋ አብርሃ ጋር በነበረው ግንኙነት የሙስና ክስ ተመስርቶበት ቢሆንም፤ ሰዎቹ ግን አጋጣሚውን በመጠቀም The Daily Monitor ጋዜጣን ዘጉ። በኋላ ላይ ፍጹምዘአብ “የጋዜጣው መዘጋት ከተከሰስኩበት ጉዳይ ጋር ግንኙነት ስለሌው፤ ጋዜጣው ስራውን እንዲቀጥል፡” ብሎ ለፍርድ ቤቱ ስሞታ ቢያቀርብም የሚሰማው አጥቶ ጋዜጣው እና የጋዜጣው ቢሮ ተዘግተው ቀሩ።
በኋላ ላይ ፍጹምዘአብ ለአምስት አመታት እድሜውን በእስር ቤት አሳለፈ። መጨዋወታችን ካልቀረ “የባከነው ግዜ” ብለን አጭር ርዕስ እንስጠውና… ከእስር የተፈታበትን አጋጣሚ እናውጋ። ዋናው አጨቃጫቂ ጉዳይ የሆነው የጉለሌ ሳሙና ፋብሪካ ጉዳይ ነበር። በእርግጥ ሃረር ማተሚያ ቤት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ንብረት ሆኖ ሳለ፤ በደርግ ዘመን ተወርሶ የመንግስት ንብረት ሆነ። በኋላ ላይ… በኢህአዴግ ዘመን ቤተ ክርስቲያኗ ማተሚያ ቤቱ እንዲመለስላት አመልክታ ሳለ፤ ሃረር ማተሚያ ቤት ለጨረታ ቀርቦ… ፍጹምዘአብ የወሰደው።
አወዛጋቢው የጨረታ ድራማ የተፈጸመው ግን በጉለሌ ሳሙና ፋብሪካ ላይ ነው። ዱጉማ ሁንዴ እና ጌቱ ገለቱ የተባሉ ትላልቅ ባለሃብቶች ፋብሪካውን ሙሉ ለሙሉ ለመግዛት 21 + ሚሊዮን ብር ይጫረቱና እ.ኢ.አ በ1989 ጨረታውን ያሸንፋሉ። ማሸነፋቸውም ይነገራቸዋል።
ሆኖም ዱጉማ ሁንዴ እና ጌቱ ገለቱ የአሸናፊነት ጽዋቸውን አንስተው ደስታቸውን ከማጣጣማቸው በፊት ደስ የማይል ወሬ ይሰማሉ። ቦርዱ ውሳኔውን ቀይሮ ‘22 ሚሊዮን ብር እና ፋብሪካውን በከፊል ባለቤት ለመሆን የተጫረተው ፍጹምዘአብ የሳሙና ፋብሪካውን እንደሚወስድ ሰምተው አዘኑ። (ከከፊል ባለቤትነት ወደ ሙሉ ይዞታንነትም ተቀየረ) ሆኖም እነዱጉማ ሁንዴ ሌላ በሚሊዮን እና በቢሊዮን የሚቆጠር ቢዝነስ ውስጥ ስለነበሩ፤ “ፋብሪካው ለፍጹምዘአብ አስገዶም ለምን ተሰጠ?” የሚል የመጨቃጨቂያ ርዕስ ከፍተው ለመካሰስ ግዜ አልነበራቸውም። በአጭሩ ጥር 5ቀን፣ 1989 ፋብሪካው ለፍጹምዘአብ ተሸጠ። አራት አመታትም ተቆጠሩ። ከዚያም በህወሃት ውስጥ የርስ በርስ ጦርነት ሲከፈት የተጠመዱት ፈንጂዎች… ከዚህም ከዚያም ይፈነዳዱ ጀመር። በዚህ አጋጣሚ የአገራችንን የፍትህ ጉድለት ያሳያልና የሳሙና ፋብሪካውን ጉዳይ ብቻ እዚህ ላይ ጠቅሰን፤ ስለጣይቱ ሆቴል ትንሽ አውግተን ማሳረጊያ እናደርጋለን።
ላለፉት አራት አመታት ምንም ኮሽ ሳይል… ሳሙናው እየተመረተ ህዝቡ በጉለሌ ሳሙና ልብሱን ማጠቡን ቀጥሏል። ዘ ሞኒተር ጋዜጣም አዲስ በተገዛው ማተሚያ ቤት በየቀኑ እየታተመች ስሟን ቀይራ The Daily Monitor ተብላለች። አዲሱ እስር ሲመጣ ሳሙናው እየተመረተ ልብሳችንን እንጠብ እንጂ፤ ውስጣችንን የሚያጥበው የእንግሊዘኛ ፕሬስ ውጤት ግን እንደተዘጋ ቀረ።
ከርዕሳችን ላለመውጣት ያህል ወደ ሳሙና ፋብሪካው እንመለስ። እናም ጉለሌ ሳሙና በስራ ላይ ሳእ፤ በአራተኛ አመቱ አቃቤ ህጉ “ግዢው ህገ-ወጥ ነው” በማለት ክስ መሰረተ። የከሳሹ አቃቤ ህግ ጭብጥ የነበረው፤ “ፍጹምዘአብ ሳሙና ፋብሪካውን በ22 ሚሊዮን ብር ሲገዛው፤ በህጉ መሰረት 40 ፐርሰንት ለባንኩ ተቀማጭ ማድረግ ነበረበት። እሱ ግን ዜሮ ተቀማጭ በማድረግ ሳሙና ፋብሪካውን ወሰደ።” የሚል ሲሆን፤ ከዚህ ጋር በተያያዘ ከአሜሪካ አገር ኒው ዮርክ ከተማ መጥቶ የመንግስት ፋይናንስ አማካሪ ሆኖ ከቆየ በኋላ የብሄራዊ ባንክ ስራ አስኪያጅ የነበረው አላዛር ደሴ ጭምር እስር ቤት ገባ። ለነገሩ አላዛር ደሴ በዚህ ምክንያት ይታሰር እንጂ፤ የእስሩ ዋና ምክንያት ወዲህ ነው።
ከአምስት አመታት በኋላ…
አቃቤ ህጉ በፍጹምዘአብ ላይ ምስክር አቀረበ። አንደኛው እና ዋነኛው ምስክር የባንኩ ኦዲተር ነበር። እናም ፍጹምዘአብ ማስቀመጥ ሲገባው ስላላስቀመጠው 40 ፐርሰንት ተቀማጭ ጉዳይ ተጠየቀ። ኦዲተሩ ግራ በመጋባት፤ “አረ አስቀምጧል።” አለ።
“አርባ ፐርሰንቱን ለባንክ ከፍሏል?” ዳኛው በመገረም ጠየቁ።
“አዎ ተከፍሏል። ይኸው መረጃው!” ፍጹምዘአብን የሚረዱ፤ 8.9 ሚሊዮን ብር የከፈለበት መረጃ ቀረበ።
አቃቤ ህጉ ገና ከመጀመሪያው መከራከሪያ ያደረገው “አርባ ፐርሰንት አልከፈለም” የሚለው ጉዳይ እዚህ ላይ አበቃ። መንግስትን በመወከል የሚከራከሩት አቃብያነ ህጎች ‘ኩም’ አሉ – አፈሩ። ፍርድ ቤቱም በፍጹምዘአብ ጉዳይ የዚያኑ ቀን ውሳኔ ሰጠ። “ፍጹምዘአብ ከዛሬ ጀምሮ በዚህ ጉዳይ ነጻ ነው” ሲል አሰናበተው። ይህ የሆነው በኢትዮጵያ አቆጣጠር ጥር 11 ቀን፣ 1998 (የዛሬ ዘጠኝ አመት ነው)
ፍጹምዘአብ ሲታሰር እንጂ ሲፈታ አገር ውስጥ ስላልነበርኩ ዝርዝር ታሪኩን እንዘለዋለን። በዚያው ዝላይ ወደድሮ ታሪክ እንሸጋገራለን።
የጣይቱ ሆቴል ነገር ሲነሳ ትንሽ ወደ ኋላ ተመልሰን በዘመኑ ዘመነኛ ስለነበረው ሆቴል ማሰባችን አይቀርም። ወደ ኢትዮጵያ የሚመጡ የውጭ አገር ሰዎች የሚያርፉበት ሆቴል አለመኖሩ፤ ሌላው ቀርቶ ከፍለው እንኳን የሚበሉበት ምግብ ቤት አለመኖሩ ያሳሰባቸው አጼ ምኒልክ ናቸው – ሆቴሉ እንዲሰራ ያደረጉት። ሆኖም ከቤት ውጪ – ሊያውም ገንዘብ ከፍሎ መብላት ስላልተለመደ ወደ ጣይቱ ሆቴል መሄድ አይዘወተርም ነበር። በኋላ ግን እንዲህ ሆነ።
አንድ እሁድ ቀን ከቤተ ክርስቲያን መልስ አራዳ ጊዮርጊስ ከሚገኘው (አሁን የአጼው ሃውልት ካለበት ስፍራ) ዋርካው ስር ችሎት ቆይተው ሲጨርሱ፤ እዚያ የነበሩትን ባላባት እና መኳንንት፤ “በሉ ከጣይቱ ሆቴል ሄደን ምሳችንን እንብላ” አሏቸው።
መኳንንቱ በፈረስ እና በበቅሎ ተከታትለው አዲስ ከተሰራው ጣይቱ ሆቴል አመሩ።
ምግብ ከመብላታቸው በፊት፤ አጼ ምኒልክ አሉ፤ “በውጭ አገር እንዲህ ያሉ ሆቴሎች ይሰሩና ሰዎች ይመገባሉ” አሏቸው። አሉና እየተበላ እና እየተጠጣ ጨዋታው ደራ።
በመጨረሻ… ከተመገቡ በኋላ የበሉት እና የጠጡት ተሰልቶ ሂሳብ ቀረበላቸው። መኳንቱ ባልጠበቁት ነገር ተገርመው ሊቆጡ የቃጣቸውም ነበሩ። ምኒልክ ግን አሉ፤ “አያቹህ… በውጭ አገር ሰው ሆቴል ከተመገበ በኋላ ሂሳብ ይከፍላል” አሉና ገንዘብ አወጡ።
ነገሩ የምር እንደሆነ ያወቁት መኳንንት፤ “የለም። መክፈል ካለብንም እኛ እንከፍላለን እንጂ፤ እርስዎ አይከፍሉም።” አሏቸው። ሂሳቡን መክፈል የሚፈልጉት ሰዎች ብዛት ሲጠየቅ ይሄም ያም እየተነሳ፤ “ዘራፍ ደሞ ለ’ቴጌ” እያለ ለመክፈል ይጋበዝ ጀመር። አጼ ምኒልክም ለመክፈል የሚጋበዙትን መኳንንት ካዩ በኋላ፤ “እንግዲህ በውጭ አገር…” ብለው ጀመሩ፤ ሁሉም ዝም ብሎ ይሰማ ጀመር።
“እንግዲህ በውጭ አገር እንዲህ በልተው፤ አንድ ሰው ሂሳብ ከከፈለ፤ ሌላው ደግሞ በተራው በሚቀጥለው ሳምንት ይከፍላል” አሏቸው። ከዚያን በኋላ በየሳምንቱ እንደ እቁብ ጣይቱ ሆቴል እየተገኙ ምሳ መገባበዝ ተለመደ። ፈረንጆችም ወደ ኢትዮጵያ ሲመጡ የሚያርፉበት እና የሚመገቡበት የመጀመሪያው ዘመናዊ ሆቴል ሆነ።
አጋጣሚውን በመጠቀም ስለ ጣይቱ ሆቴል ይቺን እንመርቅ። በሁለተኛው የኢትዮጵያ ጣልያን ጦርነት ወቅት – በጄነራል ፔትሮ ባዲዮ (በኋላ ላይ ማርሻል ሆኗል) የሚመራው ጦር ወደ አዲስ አበባ ሲገሰግስ፤ የጣይቱ ሆቴል የላይኛው ክፍል የጥቁር አንበሳ ጦር መገናኛ ሬድዮ ተሰድሮበት የሚስጥር እና ግልጽ ግንኙነት ይደረግበት ነበር። ጃንሆይ ሚያዝያ 25 ቀን፣ 1928 የአዲስ አበባ ከተማን ለቀው ሲወጡ፤ ከተማውን ራስ አበበ አረጋይ በከንቲባነት ይቆጣጠሩት በነበረበትም ወቅት ጣይቱ ሆቴል ጊዜያዊ መገናኛቸው ነበር። ጃንሆይ አዲስ አበባን ለቀው እንደወጡ አመጽ ተቀሰቀሰ፤ ዘረፋም በረከተ። የክብር ዘበኞችም በንዴት ተነሳስተው አዲስ አበባ የሚገኙ አውሮፓውያንን ማሳደድ ጀመሩ። በዚህም ግዜ ጭምር… የብዙዎቹ መሸሻ ጣይቱ ሆቴል ነበር።
ጄነራል ፔድሮ ባዲዮ አዲስ አበባ ከገባ በኋላ፤ ከሰራዊቱ ጋር አብረው የመጡት የጣልያን ጋዜጠኞች እንዲያርፉ የተደረገው ጣይቱ ሆቴል ስለነበር፤ በተለይ አንደኛ ፎቅ ላይ የነበረው፤ ድሮ ሰራተኞች የሚተኙበት አሁን ጃዝ አምባ የተሰኘው ላውንጅ የሚገኝበት ቦታ… ጣልያኖቹ ጋዜጠኞች ለጋዜጣ ህትመት የሚሆኑ ፎቶ የሚያነሱበትና የሚያትሙበት ስፍራ ነበር። እንዲህ እንዲህ እያልን የጣይቱ ሆቴል ጥንታዊ ታሪኮችን መምዘዝ ከጀመርን ቦታ እና ግዜ አይበቃንም።
ሰዎች በጣይቱ ሆቴል የየራራሳቸው ትዝታ ይኖራቸዋል። ለምሳሌ እኔ ጣይቱ ሆቴልን ሳስብ፤ ቶሎ ወደ ህሊናዬ የሚመጣው የሙያ ወንድሜ እስክንድር ነጋ ነው። መጀመሪያ Habesha የተባለ እንግሊዛኛ ጋዜጣውን፤ ከዚያም ምኒልክ ጋዜጣን ማሳተም ከመጀመሩ በፊት ጣይቱ ሆቴል እየተገናኘን ሰፊ ውይይት እናደርግ ነበር። በተለይ ምኒልክ ጋዜጣን ከመጀመሩ በፊት ጣይቱ ሆቴል ከፊል ቢሯችን ሊሆን ምንም አልቀረውም። ምሽት ላይ ፒያሳ ከመሸብንም የጣይቱ ሆቴል መኝታ ቤቶች ቤቶቻችን ነበሩ። ይህ ሁሉ ታዲያ ሆቴሉ ተሽጦ ወደ ፍጹምዘአብ ከመዛወሩ በፊት ነው። ፍጹምዘአብ ጣይቱ ሆቴልን ከገዛው በኋላ ብዙም ወደዛ መሄዳችንን አላስታውስም። ስለዚህ “ድሮ እና ዘንድሮ” በማለት ለማወዳደር እንቸገራለን። ሆኖም በቅርቡ ብዙዎችን ያነጋገረው “አትሂድ” የሚለው የሜሮን ጌትነት ግጥም እና ሌሎች ስራዎች የተቀረጹት እዚሁ ጣይቱ ሆቴል፤ ጃዝ አምባ አዳራሽ ውስጥ ነበር። (ወጋችንን እናሳርግ)
በቅርቡ አገር ቤት ደርሶ ከተመለሰ ጓደኛዬ ጋር ስንጨዋወት ጣይቱ ሆቴል ሄዶ እንደነበር አወራኝ። በዚያው ስለሆቴሉ አያያዝ ጠየቅኩት። “ኢትዮጵያ ውስጥ የአጼ ምኒልክ፣ የእቴጌ ጣይቱ እና ሌሎች ታላላቅ ኢትዮጵያውያን ፎቶ በትልልቁ ተሰቅሎ ያየሁት ጣይቱ ሆቴል ውስጥ ብቻ ነው” አለኝ።
ስለጣይቱ ሆቴል ከናንተ ጋር ያወራነውን አወራን። ፍጹምዘአብ ብቸኛ ተጫራች ሆኖ ሆቴሉን እንዴት እንደገዛው፤ ታስሮ በነበረበት ወቅት ስለነበረው ሂደት… ብዙዎች ስለማያውቁት የፍጹምዘአብ የፕሬስ አስተዋጽኦ አወራን። ከዚህ ጨዋታችን በኋላ ግን ደጋግሜ የማስብ የነበረው … ‘በሙስናም ሆነ በጉብዝና ሆቴል አንድ ግዜ በፍጹምዘአብ ስር ወድቋል። ሌላ… ምኒልክን የሚጠላ፣ የኢትዮጵያ ታሪክን የሚያጥላላ ሰው ያንን ጥንታዊ ሆቴል ገዝቶት ቢሆን ኖሮ… ምናልባት ሆቴሉን አፍርሶ ወይም፣ ስሙን ቀይሮ ሌላ ነገር ቢያደርገው ማን ጠያቂ ነበረበት? ደግሞ ባለበትም ቢሆን ጥንታዊነቱን የለቀቀ ናይት ክለብ ወይም ልብስ ቤት ወይም ስጋ ቤት ወይም ሌላ ነገር ሊሆን ይችል አልነበረምን?’ እያልኩ ደጋግሜ እያሰብኩ፤ ፍጹምዘአብንም ከነጉድለቱ መልካም ስራውን እያሞገስኩ ሳለ የጣይቱ ሆቴልን መቃጠል እንደመርዶ እሁድ ማለዳ ላይ ሰማነ።
እናም ከዚህ ቃጠሎ ጀርባ፣ በወጋገኑ ውስጥ የምናየው ፍጹምዘአብ አስገዶም ወልደሚካኤልን በቁንጽል አስተዋወቅናቹህ። ጣይቱ ሆቴልን በብላሽም ይሁን በርካሽ ገዝቶት፤ ለግዜው የግል ንብረቱ ሆኗል። ከቃጠሎው በኋላ ከማንም ባላነሰ ሳይሆን በባሰ ሁኔታ ሊያዝን ይችላል… የሚል እምነት አለን። የሱም ሆነ የሁላችንም እንባ ሊደርቅ የሚችለው ግን… ጣይቱ ሆቴል ጥንታዊ መሰረቱን ሳይለቅ እንደገና ከገነባልን ነው። እናም ሁሌም በዝምታ ውስጥ ሆኖ ትልቅ ነገር ለሚያስበው ፍጹምዘአብም እንዲህ በሉልን። “የእያሪኮ ግንብ ስለሃጢያታቸው ብዛት በእሳት ወድሞ ቀረ። የምኒልክ እልፍኝ፣ የጣይቱ ማጀት ግን እንደገና አምሮ ይሰራ። እነሆ ዘንድ መሰረቱን ጣል – ምሰሶውንም ከፍ አድርግ። እነሆ ፀሃይቱም እንደወርቅ ጠልሰም ዳግም ትድመቅ! ”
አሜን! (አሳርገናል)